Sunday, June 2, 2013

ርዕዮት ትምህርቷን ጀመረች! – ማለዳም ባይሆን አልረፈደም



ignou1











ስለሺ ሐጎስ

የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ርዕዮት በርቀት ትምህርት የማስተርስ ዲግሪዋን ለመከታተል ያቀረበችውን ጥያቄ ተቀብሎ ምዝገባውን ካከናወነች በኋላ የመማሪያ መጽሐፎች እንዳይደርሷት ከልክሎ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በዚህም ሳቢያ ከሁለት ወር በፊት ትምህርቷን መጀመር ቢኖርባትም በወቅቱ ይህ ሊሆን አልቻለም፡፡
እኛም ይህንኑ ጉዳይ ለመገናኛ ብዙሀናት አሳውቀን ነገሩ ሰፊ የዜና ሽፋን ማግኘቱን ተከትሎ ማረሚያ ቤቱ “ርዕዮት እንዳትማር የከለከላት የለም” የሚል ኦፊሴላዊ ምላሽ ሰጠ፡፡ ከማረሚያ ቤቱ ምላሽ በኋላ እኔና የርዕዮት አባት አቶ አለሙ ያለ ቦታቸው እኔቤት መደርደሪያ ላይ ለሁለት ወራት የከረሙትን  የመማሪያ መጻህፍቶች ይዘን የሚመለከታቸውን የማረሚያ ቤቱን ሀላፊዎች ለማነጋገር ወደ ቃሊቲ አመራን፡፡
“ማረሚያ ቤቱ አልከለከለም እንዲያውም ትምህርቷን በሚገባ እየተከታተለች ነው ብላችኋል፡፡ ነገር ግን ይኸው የመማሪያ መጻህፍቱ እስከዛሬ አልደረሷትም፡፡ ማረሚያ ቤቱ ይህንን ካለ ታዲያ ማ ነው የከለከለን?” የሚል ጥያቄ አቅርበን ለ3 ሰዓታት ያህል ተወያየን ወይም ተከራከርን ወይም… (የ3ቱ ሰዓታት ቆይታችን ምን እንደሚባል እንጃ ግን ቀላል ጊዜ አልነበረም) በመጨረሻ ይዘን የሄድነው የመማሪያ መጻህፍት ተመርምረው እንዲገቡላት ተስማምተን፣ ለመርማሪው አስረክበን ተለያየን፡፡
ይህ በሆነ በሳምንቱ ከትላንት በስቲያ ርዕዮት መጽሐፎቹን ተረክባ በፖለቲካል ሳይንስ ሁለተኛ ዲግሪዋን ለመከታተል አሀዱ ብላለች፡፡ ያዝልቀው እንጂ በጣም ደስ የሚል ዜና ነው፡፡ ምንም እንኳን ቀድሞም ቢሆን ልትከለከል የማይገባት መሆኑን ባውቅም፤ ኧረ እንዲያውም በማረሚያ ቤት አጥር ስር እንድትገኝ የሚያበቃት አንዳችም ወንጀል ያልፈጸመች መሆኑን ባውቅም ትምህርቷን እንድትከታተል ስለተፈቀደላት በጣም .. በጣም… ደስ ብሎኛል፡፡ ማለዳም ባይሆን አልረፈደምና!
ለነገው ብሩህ ቀናችን …ቺርስ!!!

No comments:

Post a Comment