Wednesday, July 24, 2013

የቤተ-መንግስት ደጃፍ ግፎች ፪


በእናቶች ላይ ያስጨከኑ የመደራጀት ሴራዎች
በመሐመድ ሐሰን
በአራት ኪሎ ቤተ-መንግስት አፍንጫ ስር የሚፈጸሙ ግፎች አይነታቸውና ብዛታቸው ለጉድ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ላደግንበት ኢትዮጵያዊ ባህል እጅግ በጣም እንግዳ ከመሆናቸው የተነሳ፣ ጭንቅላት አስይዘው፣ ደረት እያስደቁ ኡኡኡ…!! የሚያስብሉ ናቸው፡፡ ስርዓቱ ምን ያህል ማንነታችንን እንደሸረሸረው፣ እንዳጨካከነን፣ ሆዳም እንዳደረገን፣ ሰብአዊነታችንን እንደገፈፈው፣… ማሳያ የሚሆኑ ግፎች በአራት ኪሎ በሽ ናቸው፡፡
ለዛሬ የምናነሳቸው ግፎች ዋነኛ ማስፈጸሚያ የሆነው ቡድን ‹‹መደራጀት›› የሚል ህቡዕ ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህን ቡድን ማቋቋም ያስፈለገው፣ አንድም ግፍ የበዛበት አላማቸውን በግዚያዊ ጥቅም በመደለል በፍጥነት ማስፈጸም እና ግፋቸውን ቢያንስ በጥቅም ለደለሏቸው ቡድኖች ትክክለኛ ተግባር እንደሆነ ማሳመን ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ይህንን ቡድን በግፋቸው ውስጥ ተካፋይ በማድረግ ከምንም በላይ የበደላቸውን ሴራ ያጦዙታል፡፡ ከራሱ ከህብረተሰቡ የወጡ ወጣቶች በአከባቢያቸው፣ በአሳጋጊዎቻቸው፣ በጎረቤቶቻቸው፣ እንዲሁም በቤተሰቦቻቸው ላይ ግፍ በመፈጸም፣ የስርዓቱን ወንጀል ይጋራሉ፤ እጃቸውን ያጨቀያሉ፡፡
ስለዚህም የአራት ኪሎን ወጣት ‹‹መደራጀት›› የሚል ህቡዕ ስያሜ በተሰጠው ቡድን ውስጥ አካተው የሰፈሩን፣ የዘመዱን፣ የጎረቤቱን፣ ከፍ ሲልም የእናቱን ቤት አፍራሽ አድርገውት ቁጭ አሉ፡፡ ከዚህ ግዜ ጀምሮ እንግዲህ በግዚያዊነት ወደ ኪሳቸው የሚገባውን ገንዘብ ብቻ በማሰብ ታውረው፣ እህት ወንድሞቻቸው የዓመቱን ትምህርታቸውን እያገባደዱበት የነበረውን ትምህርት ቤት ከማፍረስ ጀምሮ፣ በአከባቢው ላይ ያገኙትን የቧንቧ ብረት እና ለመተላለፊያ መንገድነት የዋሉትን ፌሮ ብረቶች መነቃቀል፣  መሰባበራቸውን ተያያዙት፡፡ የየቀኑ ጉጉታቸውና ወሬያቸውም፣ ‹‹ ለኛ ቡድን የሚደርሰው የማን ቤት ይሆን? የስ! ብራቮ! አራት ኪሎ ሆቴል ለኛ ደረሰን፤…›› በሚሉ የአፍራሽነት ሱሶች ውስጥ ተጠመዱ፡፡ ቶሎ ቶሎ ቤቶች እንዲፈርሱ ጎትጓችም ጭምር ሆነው ተገኙ፡፡
ቡድኑ በአደገኛ የአፍራሽነት ሱስ ውስጥ ከመውደቁ የተነሳ፣ ቅንጣት ታህል ርህራሄ ራቀው፡፡ እናም ኢትዮጵያዊ ብቻ ሆነን ሳይሆን እንደ ሰውም ጭምር ስንሰማቸው የሚሰቀጥጡ የማፊያ ታሪኮች በአራት ኪሎ ለመፈጸም በቁ፡፡ ብዙዎች የሚሰሙት እና የሚያዩት ነገር የምድር ፍጻሜ (ሰምንተኛው ሺህ) ማሳያ ስለመሆኑ በእርግጠኝነት መናገር ጀመሩ፡፡ እምባቸውን አፈሰሱ፤ በአከባቢያቸው ወዳሉ የእምነት ተቋማት በመሄድም ፈጣሪያቸውን ተማጸኑ፡፡ የልጆቻቸውን እና የገዢዎቻቸውን ጤናም ጥፋትም አንድ እንዲል የመጨረሻውን ማመልከቻ፣ የመጨረሻው ቅሬታ ሰሚያችን ነው ለሚሉት ፈጣሪ አስገብተው ወደየቤታቸው ተመልሰው ሚሆነውን ዘግናኝ ግፍ ሁሉ ማየት ጀመሩ፡፡  
እነሆ ቆጥረን ከማንዘልቃቸው የግፍ ታሪኮች ውስጥ አንድ ሁለቱን እንካፈላቸው፡፡ ልብ አድርጉ! እነዚህ ታሪኮች አንዳችም ፈጠራ ያልታከለባቸው እውነቶች ናቸው፡፡ ምናልባትም እኔ የታዘብኩትን ስለማቀርብላችሁ እንጂ፣ ከነዚህ የከፉ ችግሮችም (ካሉ ማለቴ ነው) ስላለመፈጸማቸው በእርግጠኝነት መናገር አይቻልም፡፡ የኔን ግን ቀጠልኩኝ፡፡
‹‹ ልጄ አንተም ጅብ ነበርክ፣ ጅብ በላህ››
ልጅ የእናቱ ቤት በእጣ ደርሶታል፡፡ ሊኖርበት እንዳይመስላችሁ፣ ሊያፈርሰው እንጂ፡፡ ለተደራጁት ቡድኖች እጣ በሚወጣበት ወቅት፣ ይህ ባለታሪካችን ወጣት ያለበት ቡድን፣ የእራሳቸውን ቤት እንዲያፈርሱ እጣው ይወጣላቸዋል፡፡ ታዲያ የዚህ ቡድን አባላት ሳይውሉ ሳያድሩ ወደ ወጣቱ እናት ቤት ይገሰግሳሉ፡፡ እናት በልጃቸው እየተመሩ የመጡትን የሰፈር ልጆች ሲያዩ፣ አመጣጣቸው ከቤታቸው ጎራ በማለት እንደቀደመው ግዜ ሁሉ ሊጫወቱ እንደሆነ እርግጠኛ ሆነዋል፡፡
ብዙም ሳቆይ ግን እናት ግምታቸው የተሳሳተ መሆኑን ወጣቶቹ ያረዷቸዋል፡፡ ‹‹የመጣነው ቤቱን እንድናፈርስ ታዘን ነው፤›› አሏቸው፡፡ እናት በሁኔታው እጅግ በጣም ቢደነግጡም፣ የተላኩት ወጣቶች ማንነት ዳግም ሌላ የተስፋ ጭላንጭ ዘራባቸው፡፡ ከአፍራሽ ወጣቶች ውስጥ አብዛኞቹ የሳቸውን እንጀራ በሚጥሚጣ እየበሉ፣ ውሃ እና ጠላቸውን እየጠጡ ያደጉ ሲሆኑ፣ አንደኛው ደግሞ አምጠው የወለዱት የገዛ ልጃቸው ነው፡፡ ስለዚህ ቤታቸው ከመፍረስ እንደማይተርፍ ቢገባቸውም፣ ቢያንስ እንኳን ምንም ሳይስተካከል በጀሞ አከባቢ የተሰጣቸውን ቤት እስከሚያስተካክሉ እንደሚታገሷቸው እርግጠኛ ሆነዋል፡፡
በድጋሚ ሌላ የተሳሳተ ተስፋ፡፡ ወጣቶቹ ‹‹…አንዴ መጥተናል፣ ሳናፈርስ አንመለስም!›› በሚል ተዘገጃጁ፡፡ እናትን ጨምሮ ጎረቤት እና በአከባቢው የነበረው ሰው በሙሉ የሚሆነውን ማመን ከብዶታል፡፡ የልጅ ክንድ ከመከታነት፣ ወደ አፍራሽነት ተቀይሮ ማየቱ በፍጹም ሊዋጥላቸው አልቻለም፡፡ በሁኔታው ያዘነ ጎረቤት በሙሉ በየተራ ወጥቶ ከመለመን አልፎ፣ እንደፈጣሪ ተንበርክኮ ተማጸናቸው፡፡ በፍጹም ሚሰማቸው ጠፋ፤ ልጅ ከወጣቶቹ ሁሉ ብሶ ተገኘ፡፡ እናት በልጃቸው እግር ስር ተደፍተው፣ የመጨረሻ ያሉትን የአንድ ቀን እድሜ ብቻ እንዲሰጣቸው አልቅሰው ተማፀኑት፡፡ ማንም ግን ቤቱን በእለቱ ከመፍረስ ሊታደገው አልቻለም፡፡ እናት በገዛ ልጆቻቸው ጭካኔ እና ግፍ ከቤታቸው ተገፍትረው ወጥተው ከነ እቃቸው ዝናብ ላይ ተወረወሩ፡፡ በነጋታው የአከባቢው ነዋሪ ተረባርቦ፣ ለአቅመ መኖሪያነት ወዳልበቃው የጀሞ ማረፊያቸው አደረሳቸው፡፡
ልጅ በተመሳሳይ መልኩ ከሚያፈርሳቸው ቤቶች በሚያገኘው ገንዘብ ደንዝዞ፣ የመረጠውን እየበላ፣ ያሻውን እየጠጣ፣ ከፈለጋት ጋር እየተቃበጠ አለሙን መቅጨቱን ተያያዘው፡፡ ህይወት አሁን በጀመራት ‹‹ጣፋጭ›› መንገድ እንድትቀጥልለት፣ ኢትዮጵያ ሙሉ በሙሉ ፈራሽ እንድትሆንለት አጥብቆ ሳይመኝ አልቀረም፡፡ ነገር ግን ምኞቱ፣ ተራ ምኞት ብቻ በመሆኑ፣ ብዙ መስለው የታዩት የአከባቢው ቤቶች ለየቡድኖቹ እየተከፋፈሉ ፈርሰው አለቁ፡፡ እሱም እንዳሻው ሲረጨው የከረመው የግፍ ገንዘብ ያልቃል፡፡ ይሄኔ ልጅ አይኑን በጨው ያጥብና በስካር ሞቅታ ውስት ሆኖ ወደ እናቱ ቤት ያመራል፡፡  እናት በልጃቸው አይን ያወጣ ድፍረት ቢገረሙም፣ እንደሱ ግፍ ግን ፊት ለመንሳት አልቸኮሉም፡፡ በዚህ ግዜ ሁኔታውን የሚያውቁ ጎረቤቶቻቸው ኬቤታቸው ይወጡና፡
 ‹‹ደግሞ ምን ቀረኝ ብሎ መጣ?! ይህ አረመኔ!.. ታስገቢውና እንተያያለን፡፡ አንቺ ዝም ብትዪ እንኳን እኛው እንገለዋለን፡፡…›› የሚሉ የተለያዩ ዛቻዎችን ሁሉም በየበኩሉ ይሰነዝርና ያባርሩታል፡፡ እናትም ለልጃቸውን እርማቸው ቀድመው አውጥተዋልና፣ አሁን ጎረቤት የሚያደርገውን ነገር ምንም አልተቃወሙም፡፡ ልጅም አንገቱን ደፍቶ እግሩ ወደመራው ይሄዳል፡፡
በጨለማው የተባረረው ልጅ፣ እግሩ በአቅራቢያው ወደነበረ አንድ ጉራንጉር ውስጥ ይመራውና እዛው ጋደም ባለበት ጅብ በልቶት ያድራል፡፡ በመጨረሻም የልጃቸውን ሞት የሰሙት እናት፡
 ‹‹ ልጄ፣ልጄ፣… አንተም ጅብ ነበርክ፤ ጅብ በላህ፡፡›› ብለው አልቅሰው ልጃቸውን በድጋሚ ለሁለተኛ ግዜ ቀበሩት፡፡

አሮጊቷን በአምቡላንስ፣ ቤታቸውን በአፍራሽ
በአራት ኪሎ አከባቢ ይኖሩ የነበሩ አንድ እናት (አሮጊት ናቸው)፣ ቤታቸው አይናቸው ስር ባደጉ ወጣቶች ሊፈርስባቸው ሲል፣ ‹‹እንዴት ሲደረግ!›› በሚል ይከላከላሉ፡፡ ከቆይታ ቦሃላ፣ አፍራሾቹ ፖሊስ አስከትለው ተመለሱ፡፡ በአከባቢው በተፈጠረው ወከባ እና ግርግር አሮጊቷ እናት ህመማቸው ይነሳና እራሳቸውን ስተው ይዘረራሉ፡፡ ከቆይታ ቦሃላም አምቡላንስ ይመጣና ይዟቸው ወደ ሆስፒታል ይከንፋል፡፡ ይሄኔ አፍራሾቹ ምን የሚያደርጉ ይመስላቹሀል? ተደናግጠው ወደመጡበት የሚመለሱ ከመሰላቹ ተሳስታቹሀል፡፡ እነዚህ ወጣቶች ወደዚህ የአፍራሽነት ስራ ውስጥ ገና ሲገቡ ይሉኝታ፣ ባህል፣ወግ፣እንዲሁም ህሊናቸውንም ጭምር ከጫማቸው በታች በማዋል ጨፍልቀዋልና አምቡላንሱ መኪና ገና ከአይን ሳይርቅ ነበር ወዲያው ቤቱን ማፍረስ የጀመሩት፡፡
ለአብነት ያህል ከላይ ያነሳናቸውን ዓይነት ግፎች፣ በአራት ኪሎና በሌሎችም ‹‹ልማት›› የሚባል ጸረ-ደሃ እንቅስቃሴ በጎበኛቸው አከባቢዎች ላይ ማስተዋል ቀላል ነው፡፡ ጥቂት ሀብታሞች ብቻ በሚኖሩባት ሀገራችን ውስጥ የአብዛኞቹ ድሆች የየዕለት ስጋትም ‹‹መቼ ይሆን እኔስ ከቤቴ የምፈናቀለው?›› የሚል ከሆነ ሰነበተ፡፡
ከሁሉ በላይ ግን፣ እኔ በዚህ ታሪክ ውስጥ ጎልቶ የሚታየኝ እውነታ፣ ስርዓቱ በዘረጋቸው ሴራዎች ውስጥ ለመጠለፍ ያለን ዝግጁነት ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ ነው፡፡ እራሳችንን ለዚህ ሴራ ክፉኛ አመቻችተናል፡፡ ስርዓቱ ከሀገራችን አልፎ በከተማችን፣ በአከባቢያችን፣ በጎረቤታችን፣ ብሎም በራሳችን ላይ እንኳን ሲመጣ ተባባሪዎች ሆነናል፡፡ የማይነኩ ህልውናዎቻችንን የትኞቹ እንደሆኑ እንኳን መለየት እስኪሳነን ድረስ ማንነታችንን አሳልፈን ሰጥተናል፡፡ ‹‹እምቢ! አይቻልም፣ ይህንን አላደርገውም፣›› የምንልበትን ሞራል እንኳን አጥተነዋል፡፡ እና ታዲያ ይሄኔ በስርዓቱ መሰሪነት ላይ ብቻ ጣታችንን መቀሰሩ ተገቢ ይመስላቹሀል? ስርዓቱ ለመሰሪነቱ የልብ ልብ እንዲሰማው እኛስ አላገዝነው ይሆን? ምናልባት ወደ እኛ የተቀሰሩትን ጣቶች እየዘነጋናቸውም እንዳይሆን እሰጋለው፡፡
የጅቡ ታሪክ
በአራት ኪሎ አከባቢ ቤት ከፈረሰባቸው አንዱ የሆነው ብሩክ (ትክክለኛ ስሙ አይደለም) በነሱ አከባቢ ቤቶች የሚፈርሱት ከሌላው አከባቢ በተለየ አራት ኪሎ ላይ የካድሬዎችን ክፍለ ከተማ ለመገንባት ታስቦ እንደሆነ ያምናል፡፡ በተጨማሪም ብሩክ እራሱን እና የአከባቢውንም ሰው ጭምር ተጠያቂነት ለማሳየት ሁሌ የሚያነሳት አንድ ተረት አለችው፡፡ እኔ እንደተረዳኋት በራሴ መንገድ ላቅርባት፡፡
ሁለት ጓደኛሞች አብረው ተኝተው ሳለ ጅብ ይመጣል፡፡ ጓደኛሞቹ ጸጥ ብለው ተኙ፡፡ ኋላም አንደኛው ‹‹ቀርጨጭ፣ ቀርጨጭ፣…›› የሚል ድምጽ ይሰማና ጓደኛውን ‹‹ምንድነው የምሰማው ድምጽ?›› ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ጓደኛውም ‹‹ዝም በል! ጅቡ እኮ ነው፤ እግሬን እየበላው ነው፡፡›› ሲል ይመልስለታል፡፡ እግሩን ሲጨርስ ወደ ጭንቅላቱ መምጣቱን ዘንግቶት ዝምታን መምረጡ ነው፡፡
ብሩክ ይህቺን ተረት የሚያነሳት ‹‹ይበለን! የእጃችንን ነው ያገኘነው፤›› ለማለት ፈልጎ ነው፡፡ ምክንያቱን ሲያስረዳም፣ ቀደም ብሎ ከኛ በቅርብ ርቀት ላይ ይኖሩ የነበሩ ነዋሪዎች ቤታቸው በግፍ ሲፈርስ፣ ከነሱ ጋር ከመወገን ይልቅ፣ ጥጋችንን ይዘን ታዛቢ ሆነን ነበር፤ ዛሬ ያ ግፍ በኛም ላይ እንደሚደርስ ዘንግተን፤ በሚል ያንን ግዜ በቁጭት ያስታውሳል፡፡ ይህ የጁቡ ታሪክ በስንቶቻችን የህይወት ክፍል ውስጥ ስንቴ ገጥሞን ይሆን?
በአራት ኪሎ ቤተ- መንግስቱ አፍንጫ ስር የሚፈጸሙ ግፎችን ያጋራሁት አንድ ወዳጄ፡ ድርጊቱ የተፈጸመበትን ቦታ (ቤተ-መንግስቱን) እያስታወሰ፣ ‹‹ታዲያ ይሄ ምኑን ቤተ-መንግስት ነው ቤተ- ሽፍታ እንጂ›› ሲል ነበር የገለጸው፡፡ 

Tuesday, July 16, 2013

የቤተ-መንግስት ደጃፍ ግፎች 1


በመሐመድ ሐሰን
አቤት ጋዜጠኛ የመሆን እዳ! በተለይ የዚህ ዘመን ጋዜጠኝነት ፈተናው ለጉድ ነው፡፡ በአንድ በኩል እችላለሁ ያለ፡ የስራ አማራጭ ያጣ ሁሉ እየተነሳ የሚከትፍበት ሲሆን፡ በሌላ በኩል ደግሞ  ባለሙያው ከፍቃድ ሰጪው አካል እና ከመንግስት የሚደርስበት ጫና ጋዜጠኝነቱን አቀጭጮታል፡፡ በተለይ ደግሞ ማህበረሰቡ በጋዜጠኞች ላይ የሚጥለውን ተስፋ ስንመለከት፡ የቁጭታችን ልክ ጣራ ይነካል፡፡ ማህበረሰቡ ‹‹ጋዜጠኛ›› የሚለውን መጠሪያችንን እንጂ፡ የአቅማችንን፡ የሸራችንን፡ የወገንተኝነታችንን፡ የአሸርጋጅነታችንን፡… ልክ በውል አያውቀውም፡፡ ስለዚህም በደል በደረሰባቸው ፡ፍትህ በተነፈጉ ፤…ግዜ እሮሯቸውን ይዘው ወደ ጋዜጠኛ ይገሰግሳሉ፡፡ ይሄኔ በሙያው ላይ የሚወሰልቱ ‹‹ጋዜጠኞች›› የህብረተሰቡን ችግር ከሆዳቸው እና ከአለቃቸው ደስታ አንጻር በመመዘን ገሸሽ በማድረግ ተስፋ የጣለባቸውን ህብረተሰብ ሲያሳዝኑ፡ የተቀሩት ጥቂት ታማኝ ጋዜጠኞች ደግሞ አቅማቸው በፈቀደው መጠን የቻሉትን ለማድረግ ይፍጨረጨራሉ፡፡ ነገር ግን የሰፊው ማህበረሰብ ችግር በዛው ልክ ሰፊ እንደመሆኑ የየአከባቢውን ችግር በታማኝነት የሚያካፍሉን ጋዜጠኞችና የመገናኛ ብዙሀን የሉንም፡፡ ማህበረሰቡ በኢትዮጵያ ጋዜጠንነት ውስጥ ካለው አስቸጋሪ ፈተና ይልቅ ጋዜጠንነቱ ገዝፎ ስለሚታያቸው፡ አቤት ማለታቸውን አያቋርጡም፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ሰኔ 26 ቀን 2005 ዓ.ም የገጠመኝ ጉዳይ የማህበረሰቡ ተስፋ ማሳያ እንዲሁም የዚህ ጽሁፍም ጭምር መነሻ ነው፡፡
በዚሁ እለት ጠዋት ሁለት ሰዓት ተኩል ገደማ፡ አራት ኪሎ ከቤተመንግስቱ ፊት ለፊት፡ ከመኖሪያ መንደርነት ወደ ፍርስራሽ ጉራንጉርነት ወደተቀየረው ሰፈር እየዘለቅሁ ነው፡፡ የአንድ መጠነኛ የሩቅ-ለሩቅ ትውውቅ ያለን ሰው ሰላምታ ከጉዞዬ ገታኝ፡፡ ሰላምታውን ተከትሎም፡
‹‹ ለ ሀምሳ ሁለት ዓመታት ከኖርኩበት ቤቴ እኮ በግፍ ልፈናቀል ነው…›› ሲል ለወዳጅ እንኳን ረጋ ብለው ሊነግሩት የሚችሉትን ብሶት፡ ለኔ ለባዳው ምሬት በተቀላቀለበት ድምጸት ጮክ ብሎ ነገረኝ፡፡ ለምን ሊነግረኝ እንደፈለገ ግራ ገብቶኛል፡፡
‹‹እንዴት እንዲህ ሊሆን ይችላል?›› አልሁት፡፡
‹‹እኔ ምን አውቃለው? የኢህአዴግ አባል ለሆነችውና አሜሪካን ሀገር ተንፈላሳ ለምትኖረው እህቴ ብር እና ቦታ ሊሰጧት እየተስማሙ ነው፡፡…›› ሲለኝ፡ ‹‹የአባልነት ጥቅማ ጥቅም ቀበሌ ተሻግራ አሜሪካን ገባች?›› ስል በውስጤ አጉረመረምኩኝ፡፡ ቀጠል አደረግኩኝና፡
 ‹‹እንዴት ለሷ ሊሰጧት ይችላሉ?›› የሚል ጥያቄዬን አስከተልኩለት፡፡
 ‹‹እኔው በራሴ እጅ የሰጠኋት ሰነድ በእጇ ስለሚገኝ ብቻ እሷን የቤት ባለቤት አድርገው፡ እኔን ሜዳ ላይ ሊበትኑኝ ነው፡፡›. ብሶት የተጫነው ምላሹን ሰጠኝ፡፡
‹‹ለመሆኑ ቤቱ የማንና በማን ስም ነው የሚገኘው?›› የኔ ጥያቄ ነበር፡፡
‹‹ቤቱ የእናታችን ነው፤ ካርታውም በእናታችን ስም ነው፡፡›› እስረግጦ በፍጥነት መለሰልኝ፡፡
ይህ ሰው በቆይታችን ወቅት እንደነገረኝ ከሆነ፡ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ያላቸውን ቢሮዎች ሁሉ አንኳኩቶ፡ አንድም አካል ምላሽ ሊሰጠው  አልቻለም፡፡ ዛሬም ተስፋ ባለመቁረጥ በእጁ ላይ ለማስረጃነት ይሆኑኛል ያላቸውን ሰነዶች እንደያዘ እግሩ እስኪቀጥን መኳተኑን ቀጥሏል፡፡ ይህም ሰው የህብረተሰቡ አንድ አካል ነውና ይህንን ሁሉ ብሶት ለምን እንደሚነግረኝ የገባኝ ቀጣዩን ተማጽኖ ሲያቀርብልኝ ነው፡፡
‹‹እባክህ ተባበረኝ፤ አንተ ጋዜጠኛ ነህ፤…ብዙ ተበድያለው፡ ተገፍቻለው፤ ችግሬን ተካፈለኝ፡፡›› ሲል፡ እኔ ለውስጤ ‹‹በጋዜጠኛ ላይ የተጣሉ የተጋነኑ ተስፋዎች!›› የሚል ምላሽ ሰጠሁት፡፡ ተማጽኖውን እና ተስፋውን በማሰላሰል ላይ ሳለሁ፡
‹‹የአልጀዚራ ስልክ የለህም?›› አለኝ፡፡
‹‹እናፈላልጋለን አይጠፋም፡፡›› አልሁት፡፡
‹‹እባክህ ፈልግልኝ፤ ቢያንስ ቤቱን በላዬ ላይ በግፍ ሲያፈርሱት ይቅረጹኝ፤›› ሲል ተስፋ በተሟጠጠበት ስሜት ውስጥ ሆኖ ተማጸነኝ፡፡   
ከዚህ ቦሃላ ደግሞ እንደሚያገኘኝና ችግሩን ይበልጥ እንደምጋራው በማሰቡ ይመስላል፡ ከሀሳቤ ጋር ትቶኝ በቅርብ ርቀት ላይ ከነበረው የጓደኛው ቤት ዘለቀ፡፡ ዳግም ብንገናኝ ምን ልረዳው እንደምችል ባይገባኝም፡ ውስጤ ግን ጥያቄዎችን ማንሳት እና መብሰልሰሉን አላቆመም፡፡
በ አራት ኪሎ አከባቢ በአይን ብቻ እንኳን የሚታዩት ችግሮችና ግፎች ስፍር ቁጥር የላቸውም፡፡ ተገቢው ቤትና ግምት አይሰጣችሁም ተብለው እጅግ በጣም አደገኛ በሚባል ሁኔታ ውስጥ ከሚኖሩት ጀምሮ፡ እንዲሁ በዘፈቀደ ያለመጠለያ ሜዳ ላይ የመበተን አደጋ እስከተጋረጠባቸውና ሜዳ ላይ እስከወደቁት ድረስ፡ በርካታ ዘግናኝ ችግሮችን ማንሳት ይቻላል፡፡
በከተማዋ ውስጥ ከሚፈጸሙ መሰል አስከፊ ችግሮች ጋር ሲነጻጸር፡ የዛሬው ባለጉዳይ ያሰማን እሮሮ አንዱ ማሳያ ብቻ እንደሆነ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፤ ምናልባትም በአንጻራዊነት ካየነው፡ አነስተኛ ሊባል የሚችል ጉዳት ነው፡፡ ነገር ግን መቼ ነው በልማት ስም የሚፈጸሙ ግፎችና ጥፋቶች እልባት የሚያገኙት? እነዚህን ዜጎች ያላካተተ ልማት በሌላ ጎኑ ጥፋት አይሆንምን? የዜጎችን አቤቱታ ሰምቶ አሳማኝ የሆነ ምላሽ የሚሰጥ አካል መቼ ይሆን የሚኖረን? ይህን ጉዳይ የአንድ ተራ ግለሰብ ታሪክ ብቻ አድርጎ መውሰድ ፍጹም ስህተት ላይ ይጥላል፡፡ ይህ ዛሬ ታሪካቸውን ልናወራላቸው ያልተቻለን በርካታ ኢትዮጵያውያን እውነታ ነው፡፡ በየመንደሩ፡ በየሰፈሩ፡ በየቀበሌው፡ በየወረዳው፡… ጥፋቱ አድማሱን እያሰፋ ለመምጣቱ በርካታ አስረጂዎችን መደርደሩ ከባድ አይደለም፡፡ በመጨረሻም ትልቁ እና አስከፊው ሀገራዊ ውድቀት መከተሉ አይቀሬ ይሆናል፡፡
ታዲያ የሀገሪቱ ‹‹አስተዳዳሪዎች›› ከዚህ በእጅጉ የከፉ ታሪኮችን አስተውለው አያውቁ ይሆን? ዝምታቸውስ ለምና እና እስከመቼ ይቀጥላል? ጋዜጠኞችስ እንዲህ ያሉ ችግሮች ከባለስልጣናቱ መልስ (ሰበብ ብንለው ሳይሻል አይቀርም) እስካልተገኘላቸው ድረስ አፍነን የምናቆየው እስከመቼ ነው? ከአለቆቻችን ከንቱ ውዳሴ ይልቅ በመከራ ውስጥ ያሉ ዜጎችን ድምጽ መቼ ይሆን የምንሰማው? ህብረተሰቡ በጋዜጠኞች ላይ ያነገበው ተስፋ ከመክሰሙ በፊት መታደግ ይቻል ይሆን? ምላሹን ለየራሳችን እንተወው፡፡
ከሁሉ በላይ ደግሞ ባለታሪካችንን ጨምሮ፡ ሌሎች ዘልቀን የማንጨርሳቸው ግፎች እና በደሎች የሚፈጸሙት፡ ከሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መቀመጫ (በቤተ-መንግስቱ) አፍንጫ ስር መሆኑ ነው፡፡ አፍንጫቸው ግን ይህንን እንኳን ማሽተት የቻለ አይመስልም፡፡ እና ይህንን ካላሸተተ ሌላውን ስስለማሽተቱ በምን እርግጠኛ መሆን ይቻላል? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ ምናልባት በመካከላቸው ላይ ያለው ብቸኛው የአስፓልት መንገድ፡ ኑሯቸውንና ህይወታቸውን የየቅል አድርጎ ከፍሎት፡ የድሆቹ ድምጽ አልሰማ ብሏቸውም ይሆናል፡፡ አስፓልት እና ወታደር በለየው አንድ ግቢ ውስጥ እየኖሩ ላለመተያየት፡ ላለመሰማማት፡ ላለመረዳዳት፡ ላለመተዛዘን፡ ላለመግባባት፡ላለመደማመጥ፡ ላለመነጋገር፡  … መወሰን መቻል መጨረሻችንን የት ያደርሰው ይሆን?


ከጥቁሩ ጋዋን በስተጀርባ



መሐመድ ሐሰን



በቀደሙት ግዚያት የነበሩ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ስናስብ በርካታ ጠንካራ ጐኖቻቸው ወደ እዝነ ህሊናችን ይመጣሉ፡፡ በተለይ ከንባብ እና የሙግት ባህላቸው ጋር በተያያዘ፣ ከወቅት እማኞች የምንሰማው እውነታ አስገራሚ ሊባል የሚችል ነው፡፡ በየጥጋጥጉ፣ በየመማሪያ ክፍሉ፣ ወዘተ የሚደረገው ውይይት መነሻው መፅሐፍ ሲሆን፣ ታላላቅ ፀሐፊዎችም እንደጉድ ይጠቃቀሳሉ:
 ውጤቱ ላይ ሰፊ ክርክሮች የሚስተጋቡ ቢሆንም እነዚህ የቀደሙት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለኢትዮጵያ ይበጃል ባሉት ሀሳብ ላይ ተሳትፈዋል፤ ተሟግተዋል፣ ታግለዋል፡፡ የሀገራችን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳይ ያገባናል ይመለከተናል በሚል ያመኑበትን ሀሳብ አቀንቅነዋል፡፡
ብዙም ወደኋላ ርቀን ሳንሄድ የታላላቆቻችንን የቅርብ ግዜ ትዝታዎችን ለማስታወስ ብንሞክር እንኳን ብዙ እውነታዎች ይገለጡልናል፡፡ የርዕስ ጉዳያቸው ማጠንጠኛ ሀገራዊ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ጉዳዮች ሲሆኑ ምክንያቶቻቸውም ልፍስፍስ የሚባሉ አልነበሩም፡፡
ዛሬስ ?
ዛሬ ዛሬ በዩኒቨርስቲዎቻችን ውስጥ ያለው ሁኔታ ከቀደሙት ግዚያት የተለየና ሌላ አሳፋሪ መልክ እየያዘ ከመጣ ሰንበትበት አለ፡፡ ለሚነሱት ግጭቶች መንስኤው ብሔር ነው፡፡ በብዛት ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በአካዳሚያዊ ነፃነቶች ላይ ተሟግቶና ተከራክሮ በሀሳብ ፍጭቶች ከመተማመን ይልቅ፣ ብሔሬ ተነካ በሚል ሰበብ ብቻ መበጣበጥ፣ የዚህ ዘመን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አሳፋሪው መገለጫ ሆኗል፡፡ ከዚህ ውጪ በአሁኑ ሰዓት በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ግጭቶች ከተነሱ መነሻቸው “ወጥ ቀጠነ፣ እንጀራው ሳሳ፣ ዳቦው ጠቆረ፣ ወዘተ” የሚሉ ሆድ ተኮር ተልካሻ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ዩኒቨርሲቲዎቻችንም ሀገራዊ ጉዳይ ግድ የማይሠጣቸው “ምሁራንን?” ማምረታቸውን አጠንከረው የቀጠሉበት ይመስላሉ፡፡ እንዲህ ያሉ ተመራቂዎች ነገ በከፍተኛ የሀላፊነት ደረጃ ላይ ሲቀመጡ ሊፈጥሩ የሚችሉትን ሀገራዊ ቀውስ ማሰቡ ብዙም ከባድ አይሆንም፡፡
በዚህ ዘመን በዩኒቨርሲዎቻችን ውስጥ ለሚስተዋሉ ዝቅጠቶች የትምህርት ፖሊሲው እና ፅንፈኝነት እንደ ምክንያት ከሚጠቀሱት ውስጥ ዋነኞቹ ናቸው፡፡ የሚሰጠው ትምህርት በጥናትና ምርምር ላይ ያልተመሰረተ መሆኑ፣ ለተማሪው የሚሰጠው ድጋፍ እና የተማሪዎቹ ውጤት ዝቅተኝነት፣ የትምህርት ጥራቱን የሚያረጋግጥ ተቋም አለመኖር፡ የአስተማሪዎቹ ብቃት ማነስ እና ሌሎችም ተያያዥ ነጥቦች ለዩኒቨርሲቲዎቻችን ውድቀት እንደማሳያነት የሚቀርቡ ናቸው፡፡
አንድ የትምህርት ተቋም በተማሪዎቹ መካከል የሀገራዊ ማንነትን ስሜት፣ ባህላዊ መከባበርን፣ መረዳዳትን፣… መፍጠር እንዳለበት ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡ የኛ ሀገር የትምህርት ስርዓት ግን ከዚህ በተቃራኒ፣ በተማሪዎች መካከል መራራቅን፣ መጠላላትን፣ ስጋትን እና ጥርጣሬን በተማሪዎች መካከል እያነገሰ እንደሆነ ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ በየትምህርት ተቋማቱ ያሉ የአስተዳደር አካላትም ጉዳዩን ችላ በማለት ተማሪው ሲደናቀፍ ከጥግ ቆመው መታዘብን የመረጡ ይመስላሉ፡፡
ሰሞነኛ ምርቃቶች
ይህ ወቅት ከምርቃት ፕሮግራሞችጋር በተያያዘ ዩኒቨርሲቲዎችና ተመራቂ ተማሪዎቻቸው ሽር ጉድ የሚሉበት ነው፡፡ አንዳንዶችም ማስመረቅ ጀምረዋል፡፡ ሆኖም ግን በተማሪዎቹ ላይ በርከት ያሉ ጥያቄዎች መነሳታቸው አልቀረም፡፡ እውን እነዚህ ተማሪዎች ብቁ ሆነው ነው የሚወጡት? የእውቀታቸው ልክስ እስከየት ይደርሳል? የስራ ዋስትናቸው ምን ይመስላል? በዩኒቨርሲቲዎቻችን ውስጥ ሳሉ ምን ሰሩ? ምንስ ይሰሩ ነበር? መሰረታዊ ፍላጐታቸውስ ምንድነው? ወዘተ የሚሉ ማቆሚያ የሌላቸው ጥያቄዎች በዘመኑ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ላይ የሚነሱ ናቸው፡፡ ለትምህርታቸው ተጨማሪ አስረጅ የሚሆኗቸውን መጽሀፍትን እና ከትምህርት ውጪ ያሉትን የህትመት ውጤቶች ለማንበብ ያላቸው ተነሳሽነትም ትልቅ ጥያቄ የሚነሳበት ነው፡፡
የማይስማሙ ተማሪዎች
ተማሪው በግቢ ውስጥ ተስማምቶ ለመኖር በወንዛዊነት፣ በፓርቲ አባልነት፣ በሀይማኖት፣ ዝቅ ሲልም በዲፓርትመንት (ትምህርት ክፍል)፣ መቧደኑ ግድ እየሆነ ለመምጣቱ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ ተማሪውን አንድ የሚያደርገው ጉዳይ ማግኘት የሰማይ ያህል ርቋል፡፡ የ “ቶም እና ጄሪ” ባህሪ መገለጫቸው የሆነው ተማሪዎቹ፣ በአንድ ትምህርት ክፍል ውስጥ ሁለት ቲሸርት፣ መፅሔት፣ ጉዞ፣… ማዘጋጃ እየተለመደ መጥቷል፡፡ የአዲስ አበባና የክፍል ሀገር ልጆች በመባባል መቧደንም የዚህ ዘመን እጩ “ምሁራን” መገለጫ ነው፡፡  
የፓርቲ “አባልነት” የስራ ዋስትና
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲት ስድስት ኪሎ ካምፓስ ውስጥ ከሚገኘው ባህል ማዕከል በርከት ያሉ ተማሪዎች በመውጣት ላይ ናቸው፡፡ “ላንተ ምን ተሰጠህ? ላንቺ ምን ተሰጠሸ?” በሚል አፍ ለአፍ ገጥመው ሁሉም ይንሾካሾካሉ፡፡ ተማሪዎቹ በጉጉት እየተጠያየቁ ያሉት በፓቲያቸው ውስጥ ስለሚሰጣቸው “ኤ” እና “ቢ” እንዲሁም አፈንጋጭ የተባሉት አባላት ስለሚያገኙት “ሲ” ነው፡፡ መምህሮቻቸው ከሚሰጧቸው “ኤፍ” ይልቅ፣ ከፓርቲያቸው በአባልነት የሚሰጣቸው “ሲ” ህይወታቸውን እንደሚያጨልመው ይሰማቸዋል፡፡ በአሁን ሰዓት የፓርቲ አባልነት፣ የስራ ዋስትና የመሆን ተስፋው ተሟጦ ስለማለቁ የሚናገሩት አባላቱ እራሳቸው ናቸው፡፡ እውነት ኢህአዴግ ለአባላቱ በሙሉ ስራ ይሰጣል? መስጠትስ ይችላል? ይህንን ሁሉ አባል የማስተናገድ አቅሙስ ምን ያህል ነው? የአባላቱ መብዛትስ የስራ ዋስትና የመስጠት አቅሙን አልተገዳደረው ይሆን? . . ከብዙዎች የሚነሳ ጥያቄ ነው፡፡ ብዙዎችም ተስፋ የቆረጡ ይመስላሉ፡፡
በግቢ (ዩኒቨርሲቲ) ውስጥ በሚኖራቸው ቆይታ ከተራ አባልነት እስከ ሀላፊነት ኢህአዴግን ሲያገለግሉ የነበሩ ሰዎች በስራ ማጣት ሲንገላቱና በመጨረሻም ከተመረቁበት የትምህርት መስክ ውጪ፡ እንደ አስተማሪነት ባሉ ስራዎች ላይ ሲሰማሩ እያየን ነው፡፡ ይህም አባልነት የስራ ዋስትና መሆኑ እያከተመ ለመምጣቱ ጥሩ ማሳያ ሳይሆን አይቀርም፡፡ አብዛኞቹ ደግሞ ሳያምኑበት ለስራ በሚል ብቻ ህሊናቸውን ሸጠው አባል እንደሆኑ ይነገራሉ፡፡ ያም ሆኖ ግን ስራውን ማግኘት አልተቻላቸውም፡፡ ማን ነበር “ጮማ እየበላሁ ማሰብ ከማቆም ቆሎ እየቆረጠምኩ ባስብ ይሻለኛል፡፡” ያለው?
ምን ተይዞ ጉዞ?
ከሱፉ እና ከጋዋኑ ስር ያለው የተማሪዎቹ ማንነት ግልፅ አይደለም፡፡ ነገር ግን ወደፊት የሚጠበቅባቸውን ህይወት እና የሚያገለግሉትን ማህበረሰብ ስናስብ ብዙ ነገር እንድንጠይቅ እና እፍረት እንዲሰማን እንሆናለን፡፡ በቅጡ እውቀት ሳይጨብጡ የሚመረቁ ተማሪዎች ማህበረሰቡ ውስጥ ገብተው ሊያገለግሉና ሊያስተምሩ? ወይስ በድጋሚ ለሀገር ሸክም በመሆን ማህበረሰቡ ሊያገለግላቸውና ሊያስተምራቸው?
በ2001 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጋዜጠኝነት ትምህርት ክፍል ተመራቂ ተማሪዎች በቲሸርታቸው ላይ “Never stop Asking” የሚል ፅሁፍ አስፍረው እንደነበረ አስታውሳለሁኝ፡፡ ነገር ግን የለበሱትን ተማሪዎች ጨምሮ፡ የአሁን ግዜ ተመራቂዎች (በተለይ በጋዜጠኝነት ትምህርት ክፍል ውስጥ ያሉት) በድፍረት ጥያቄዎችን ስለማንሳታቸው ብቻ ሳይሆን፣ ስለማንበባቸው እና ስራቸውን በአግባቡ ለመወጣት ስለመፃፋቸው አፍን ሞልቶ መናገሩ ይከብዳል፡፡
በአንድ ወቅት ለሀገራዊ ጉዳች ሀገራዊ ምሳሌዎችና ተረቶች ከማይነጥፉበት ምሁር ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጋር ስንጨዋወት ያካፈለኝን ወግ እዚህች ጋር ብጠቅሰው ተገቢ መስሎ ይሰማኛል፡፡ ሰውዬ አሁን ስማቸውን በውል የማላስታውሳቸው የአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመነ መንግስት ባለስልጣናት ናቸው፡፡ እናም እኚህ ባለስልጣን ከግራዝማቾችና ቀኝ አዝማቾች ጋር በመጋጨታቸው፣ ነጋዴውን ሁሉ እያሰጠሩ የቀኝ አዝማችነት እና የግራአዝማችነት ማዕረግን በማደል ሀገሩን በሙሉ አጥለቀለቁት፡፡ ከዛ በኋላ ማዕረጉ ረከሰ፡፡ አሁንም ኢህአዴግ ይህንኑ ስልት በመከተል ሀገሪቱን በሙሉ በድግሪ ምሩቃን፣ በዶክተሮች እና በፕሮፌሰሮች በማጥለቅለቅ ት/ትን ዋጋ ማሳጣት የፈለገ ይመስላል፡፡ ይህ አካሄድ የስርዓቴ ተቃዋሚ ናቸው የሚላቸው ምሁራንን ለማጥቂያነት ቢያውለውም፣ ውጤቱ ግን ለሀገራዊ ውድቀት እንደሚዳርገን ከፍንጭ በላይ የሆኑ እውነታዎችን ማየት ከጀመረን ሰነበተ፡፡ ለሁላችንም ስለ ሀገር የማሰብ ልቦናውን እንዲሰጠን መመኘቱ ሳይሻል አይቀርም፡፡ ለማንኛውም ወጉ እንዳይቀርብኝ ለተመራቂዎች እንኳን ደስ ያላችሁ ብያለው፡፡  

ስጋት የተጫነው የቤት ባለቤትነት ተስፋ


               በመሐመድ ሐሰን
አዲስ አበባን ለኑሮ የማትመች ሲኦል ካደረጓት ምክንያቶች ውስጥ አንዱና ዋነኛው ቤት የማግኘት ችግር ነው፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ ገንዘብ ከፍሎ እንኳን ቤት ማግኘት በጣም አታካች ከመሆኑም ባሻገር: ከቤቶቹ ጥራትና ዋጋ ጋር በተያያዘ የሚነሳው ቅሬታም ቢሆን ከኢትዮጵያዊነት ስብዕና የራቀ ግፍ የሚፈጸምበት ነው፡፡ እንዲህ ያለው ቀዳሚና ግዙፍ ችግር መፍትሄ ሊበጅለት ነው ሲባል ደግሞ የህዝቡ በተስፋ መሞላት እና መፈንጠዝ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከሰሞኑ የንግድ ባንኮችን እና ቀበሌዎችን አጨናንቆ የተመለከትነው ሰልፍም የዚሁ ተስፋ ማሳያ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን የከተማዋን ዋነኛ ችግር ለመቅረፍ የተወጠነው እቅድ በጎ ስለመሆኑ ማንኛውም ሰው ይስማማል፡፡ ነገር ግን በተስፋ ከተጨናነቁት ሰልፎች ውስጥም ቢሆን የሚነሱት ስጋቶችና ጥያቄዎች፡ ውሃ የማይቋጥሩ ናቸው በሚል እንደ ቀልድ የሚታለፉ አይደሉም፤ ለተጨማሪ እይታ በር የሚከፍቱ እንጂ፡፡

በፖለቲካ የተጠለፈ ተስፋ?
በ1997 ዓ.ም የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ ቤት)  ምዝገባ ሲካሄድ፡ ጉዳዩን ከፖለቲካ ጋር በማያያዝ ሳይመዘገቡ የቀሩ በርካቶች ነበሩ፡፡ አሁን የተጀመረውን አዲሱ ምዝገባም ቢሆን ከፖለቲካው ጋር ያያዙት ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ጉዳዩን በበላይነት ይዘነዋል የሚሉ የስራ ሃላፊዎችም፡ በሰሞነኛው የቤት ባለቤትነት ጉዳይ ላይ የተለያየ ሀሳብ የሚሰነዝሩ መገናኛ ብዙሀንን፡ የፖለቲከኛ አለቆቻቸውን አፍ በመዋስ ‹‹ተላላኪ›› ሲሉ አድምጠናል፡፡ 
ጉዳዩን ከፖለቲካው ጋር የሚያያይዙት ሰዎች በቀዳሚነት የሚያነሱት ከምርጫ ጋር የተያያዘውን ነጥብ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ፡ ‹‹የዚህች ሀገር ብቸኛው ልማት አብሳሪ እኔ ነኝ፡ እኔ ከሌለው ሀገሪቱ ትበታተናለች፡…›› ከሚለው ልማዳዊ ዲስኩሩ በመነሳት፡ አሁን የሚጀመረውን የቤት ግንባታ ፕሮግራምም ከሱ ውጪ ሌሎች እንደማይጨርሱት ማሳመን ይፈልጋል ሲሉ ይወቅሱታል፡፡ ባለስልጣናቱም ከዚሁ ስጋት ጋር በተያያዘ ለህብረተሰቡ ግልጽ ያለ መረጃ በማቀበል ዋስትና መስጠት የሚፈልጉ አይመስሉም፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ግንባታው ከተያዘለት የግዜ ገደብ በመነሳት፡ ሂደቱን ለቀጣይ ሁለት ምርጫዎች የተከፈለ ቀብድ ነው የሚለውን ሀሳብ አጠንክሮታል፡፡ እንዲህ ያለው የፖለቲካ ጨዋታ ደግሞ ህዝቡን ለተጨማሪ የባርነት እና እስረኛነት ህይወት መዳረጉ እሙን ነው፡፡ ከዚህ ስትራቴጂ በመነሳትም ‹‹ቁሳዊ ሀብትን ብቻ በማብሰር እስከመቼ እያበሉ መግዛት ይቻላል?›› የሚለው ጥያቄ ተያይዞ ይነሳል፡፡
ፓርቲውና ባለስልጣናቱ መሬት ሲቸበችቡ እና ቤት ሲሰሩ በመኖራቸው፡ ህዝቡ ውስጥ ያለውን ብሶት ለማስተንፈስ በሚል የሰሞኑ ተስፋ ሆን ተብሎ እንደተፈጠረ የሚጠረጥሩም አሉ፡፡ ምሁራን እና ተቃዋሚዎችም በጉዳዩ ላይ አማራጮችን በመጠቆም ዋስትና ከመስጠት በመቆጠባቸው ከህዝቡ ትችት አላመለጡም፡፡
ጉዳዩን በበላይነት የሚቆጣጠሩት ሰዎች ከፖለቲካው ነጻ ናቸው ተብሎ ስለማይታመን፡ የፓርቲው አባላት በተለያየ መንገድ ከግናባታው ሂደት ብቸኛ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ሊደረግ የሚችልበት እድልም ሰፊና ብዙዎች የሚጋሩት ስጋት ነው፡፡ ከቀደሙ ተሞክሮዎች በመነሳት መናገር እንደሚቻለው፡ ለስራው የሚያስፈልጉ ግብአቶች በሙሉ በፓርቲው ስር የተደራጁ አባላት እንዲያቀርቡ ይደረጋል፤ ከጥቃቅን የመንገድ ስራዎች ጀምሮ እስከ ቤቶቹ ግንባታ ድረስ ያለው ስራም ለአባላቱ ተመርጦ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ ጉዳዩን ከሀገራዊነት ወደ ፓርቲያዊነት ያወርደዋል፡፡
ያልተመለሱ ጥያቄዎች
ከፖለቲካዊ አንድምታው በበለጠ አዲሱ የቤቶች ልማት ፕሮግራም በርካታ ያልመለሳቸው ውስብስብ ጥያቄዎች ይነሱበታል፡፡ ከሁሉም በላይ ከምዝገባው ሂደት እንኳን ቀድሞ የሚነሳው ጥያቄ፡ በልማት ስም ከተሰሩት እና ወደፊትም ከሚሰሩት ግፎች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ጥቂት ኮሚቴዎችን ብቻ በጥቅም አስሮና አሳምኖ የአንድን መንደር ነዋሪ በሙሉ ለከፋ ችግር ከመዳረግ፡ ከአሁኑ ተጠያቂነት ያለበት አሳማኝ ስራ ለመስራት ማሰቡ የተሻለ ነው፡፡ ነዋሪዎችን በልማት ስም አፈናቅሎ መልሶ ነገ ወደሚፈርስ ቦታ እያዘዋወሩ እንደተከራይ ማንከራተት ለከፍተኛ ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማህበራዊ ቀውስ እንደሚዳርጋቸው የምር መታሰብ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ ቀደም ‹‹ለልማት›› ተፈናቃዮች የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ) ቤት  ያለ እጣ  ቀድሞ እንዲሰጣቸው የሚደረግበት አሰራር ነበር፡፡ ወደፊትስ ተመዝግበው ቤት የሚጠብቁ ሰዎችን እጣ ከማራዘም፡ በልማት ስም ለሚነሱ ነዋሪዎች እራሱን የቻለ ተጠባባቂ መኖሪያ በመገንባቱ በኩል ምን አይነት እቅድ ተይዞ ይሆን የሚለው ጥያቄ መልስ የሚሻ ነው፡፡
ከቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት ምዝገባ ጋር በተያያዘ እንደ ዋዛ ሊታለፉ የማይገባቸው ጉዳዮችም አሉ፡፡ ወደ አራት መቶ ሺህ (400.000) ሰው ተመዝግቦበታል የሚባለው የቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት አንድ መቶ ሺህ (100.000) ለሚሞሉ ነዋሪዎች እንኳን አልተዳረሰም፡፡ በነዚህ ሁሉ ዓመታት ይህቺን ብቻ ከሆነ ማሳካት የተቻለው፡ በቀጣይ እየታሰበ ያለው ፕሮግራምስ በተባለው ግዜ ለመድረሱ ምን ዋስትና አለው? የቀድሞ ተመዝጋቢዎች ፋይል ጠፋ መባሉ ምንድነው የሚነግረን? በቀጣይ የተመዘገቡ ሰዎችስ ዋስትናቸው ምንድነው? እስኪጣራ እንደ አዲስ መመዝገባቸውስ ቦሃላ የሚጣራበት መንገድ ስለመኖሩ ዋስትና ይሰጣል? ቀድሞ የመመዝገብ እድሉን አግኝተው የነበሩ ነገር ግን አሁን የተባለውን ገንዘብ መቆጠብ የማይችሉ ነዋሪዎች እየገጠሙን ነው፤ የነሱስ ተስፋ ምንድነው?
ከቤት ልማት ጋር በተያያዘ የሚሰሩ መስሪያ ቤቶች ለሙስና የተጋለጡና በተለያየ ግዜም እንደሚቀያየሩ ይታወቃል፤ ታዲያ ህዝቡ አዲሱን ፕሮግራም እንደሚያስፈጽሙ እንዴት እምነት ሊጥልባቸው ይችላል? ከግል ተቋራጮች ጋር ያለው የዋጋ ልዩነትና ቤቱን መረከቢያ የግዜ ምጣኔ መንግስት ካቀረበው ጋር ያለው ልዩነት ተመዛዝኖ ይሆን? ህብረተሰቡ የሚጠይቃቸው ጥያቄዎች ናቸው፡፡
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ባለፈው ቅዳሜ ለአዲስ ጉዳይ መጽሄት (ቅጽ7 ቁጥር 169 ሰኔ 005) በላከው ደብዳቤ ላይ እንደገለጸው ‹‹…ዋናው ጉዳይ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ተነድፏል ወይ? የሚለው  ጥያቄ በአግባቡ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ማረጋገጡ ነው፡፡…›› ይላል፡፡ እኔ ግን ይህንኑ ጥያቄ መልሼ ለራሱ ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መጠየቅ እወዳለው፡፡ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ስለመነደፉ ምን ያህል እርግጠኞች ናችሁ? ዋስትናስ መስተት ይቻላቹሀል? መልሱን ተጨባጭ በሆነ መረጃ ብታሳዩን መልካም ነው፡፡
ይሕው ከላይ የተጠቀሰው ደብዳቤ ‹‹ዓላማችን ከተሞቻችንን የልማት የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ማዕከላት ማድረግ ነው!!›› የሚል መልዕክት በመዝጊያው ላይ አስፍሯል፡፡ እውነት በከተማችን ውስጥ የምናያቸው ከቤት ግንባታና መልሶ ማልማት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ከላይ የተጠቀሱትን የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ዓላማዎች  (ልማት፡ዲሞክራሲና መልካም አስተዳደር) የሚያሟሉ ናቸው? በልማት ሰበብ የተፈናቀሉትን በአግባቡ አለማስፈር፡ በከተማዋ ውስጥ ያለው የቤት ችግር በአግባቡ ካልተቀረፈ፡ በመስሪያ ቤቱና በነዋሪው ዘንድ መግባባትና መተማመን ካልተፈጠረ፡… ከተዘረዘሩት ውስጥ የትኛውን አላማ ለማሳካት  እንደምትጥሩ ማወቁ ያጓጓል፡፡
አንድ ወዳጄ የሰሞኑን የቤት ባለቤትነት ምዝገባ ይፋ መደረግ ተከትሎ  ‹‹ቆጥ ላይ ከማደራችን በፊት ደረሱልን›› ነበር ያለው፡፡ በእርግጥ አሁንም ህብረተሰቡ እንደደረሳችሁለት እርግጠኛ መሆን ይፈልጋል፡፡ እንደኔ እምነት አዲስ አበባ ላይ ማደሪያ ቆጥ እንኳን በአማራጭነት ስለመገኘቱ በእርግጠኝነት መናገር ይከብደኛል፡፡ወዳጄ ግን ከ‹‹ደረሱልን›› ወደ ‹‹ደረሱብን›› ከመሸጋገሩ በፊት  ችግሩን የምር መረዳትና ተጨባጭ መፍትሄ መፈለጉ ለሁላችንም ሳይበጀን አይቀርም፡፡                          

ስጋት የተጫነው የቤት ባለቤትነት ተስፋ


በመሐመድ ሐሰን
አዲስ አበባን ለኑሮ የማትመች ሲኦል ካደረጓት ምክንያቶች ውስጥ አንዱና ዋነኛው ቤት የማግኘት ችግር ነው፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ ገንዘብ ከፍሎ እንኳን ቤት ማግኘት በጣም አታካች ከመሆኑም ባሻገር: ከቤቶቹ ጥራትና ዋጋ ጋር በተያያዘ የሚነሳው ቅሬታም ቢሆን ከኢትዮጵያዊነት ስብዕና የራቀ ግፍ የሚፈጸምበት ነው፡፡ እንዲህ ያለው ቀዳሚና ግዙፍ ችግር መፍትሄ ሊበጅለት ነው ሲባል ደግሞ የህዝቡ በተስፋ መሞላት እና መፈንጠዝ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከሰሞኑ የንግድ ባንኮችን እና ቀበሌዎችን አጨናንቆ የተመለከትነው ሰልፍም የዚሁ ተስፋ ማሳያ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን የከተማዋን ዋነኛ ችግር ለመቅረፍ የተወጠነው እቅድ በጎ ስለመሆኑ ማንኛውም ሰው ይስማማል፡፡ ነገር ግን በተስፋ ከተጨናነቁት ሰልፎች ውስጥም ቢሆን የሚነሱት ስጋቶችና ጥያቄዎች፡ ውሃ የማይቋጥሩ ናቸው በሚል እንደ ቀልድ የሚታለፉ አይደሉም፤ ለተጨማሪ እይታ በር የሚከፍቱ እንጂ፡፡
በፖለቲካ የተጠለፈ ተስፋ?
በ1997 ዓ.ም የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ ቤት)  ምዝገባ ሲካሄድ፡ ጉዳዩን ከፖለቲካ ጋር በማያያዝ ሳይመዘገቡ የቀሩ በርካቶች ነበሩ፡፡ አሁን የተጀመረውን አዲሱ ምዝገባም ቢሆን ከፖለቲካው ጋር ያያዙት ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ጉዳዩን በበላይነት ይዘነዋል የሚሉ የስራ ሃላፊዎችም፡ በሰሞነኛው የቤት ባለቤትነት ጉዳይ ላይ የተለያየ ሀሳብ የሚሰነዝሩ መገናኛ ብዙሀንን፡ የፖለቲከኛ አለቆቻቸውን አፍ በመዋስ ‹‹ተላላኪ›› ሲሉ አድምጠናል፡፡ 
ጉዳዩን ከፖለቲካው ጋር የሚያያይዙት ሰዎች በቀዳሚነት የሚያነሱት ከምርጫ ጋር የተያያዘውን ነጥብ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ፡ ‹‹የዚህች ሀገር ብቸኛው ልማት አብሳሪ እኔ ነኝ፡ እኔ ከሌለው ሀገሪቱ ትበታተናለች፡…›› ከሚለው ልማዳዊ ዲስኩሩ በመነሳት፡ አሁን የሚጀመረውን የቤት ግንባታ ፕሮግራምም ከሱ ውጪ ሌሎች እንደማይጨርሱት ማሳመን ይፈልጋል ሲሉ ይወቅሱታል፡፡ ባለስልጣናቱም ከዚሁ ስጋት ጋር በተያያዘ ለህብረተሰቡ ግልጽ ያለ መረጃ በማቀበል ዋስትና መስጠት የሚፈልጉ አይመስሉም፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ግንባታው ከተያዘለት የግዜ ገደብ በመነሳት፡ ሂደቱን ለቀጣይ ሁለት ምርጫዎች የተከፈለ ቀብድ ነው የሚለውን ሀሳብ አጠንክሮታል፡፡ እንዲህ ያለው የፖለቲካ ጨዋታ ደግሞ ህዝቡን ለተጨማሪ የባርነት እና እስረኛነት ህይወት መዳረጉ እሙን ነው፡፡ ከዚህ ስትራቴጂ በመነሳትም ‹‹ቁሳዊ ሀብትን ብቻ በማብሰር እስከመቼ እያበሉ መግዛት ይቻላል?›› የሚለው ጥያቄ ተያይዞ ይነሳል፡፡
ፓርቲውና ባለስልጣናቱ መሬት ሲቸበችቡ እና ቤት ሲሰሩ በመኖራቸው፡ ህዝቡ ውስጥ ያለውን ብሶት ለማስተንፈስ በሚል የሰሞኑ ተስፋ ሆን ተብሎ እንደተፈጠረ የሚጠረጥሩም አሉ፡፡ ምሁራን እና ተቃዋሚዎችም በጉዳዩ ላይ አማራጮችን በመጠቆም ዋስትና ከመስጠት በመቆጠባቸው ከህዝቡ ትችት አላመለጡም፡፡
ጉዳዩን በበላይነት የሚቆጣጠሩት ሰዎች ከፖለቲካው ነጻ ናቸው ተብሎ ስለማይታመን፡ የፓርቲው አባላት በተለያየ መንገድ ከግናባታው ሂደት ብቸኛ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ሊደረግ የሚችልበት እድልም ሰፊና ብዙዎች የሚጋሩት ስጋት ነው፡፡ ከቀደሙ ተሞክሮዎች በመነሳት መናገር እንደሚቻለው፡ ለስራው የሚያስፈልጉ ግብአቶች በሙሉ በፓርቲው ስር የተደራጁ አባላት እንዲያቀርቡ ይደረጋል፤ ከጥቃቅን የመንገድ ስራዎች ጀምሮ እስከ ቤቶቹ ግንባታ ድረስ ያለው ስራም ለአባላቱ ተመርጦ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ ጉዳዩን ከሀገራዊነት ወደ ፓርቲያዊነት ያወርደዋል፡፡
ያልተመለሱ ጥያቄዎች
ከፖለቲካዊ አንድምታው በበለጠ አዲሱ የቤቶች ልማት ፕሮግራም በርካታ ያልመለሳቸው ውስብስብ ጥያቄዎች ይነሱበታል፡፡ ከሁሉም በላይ ከምዝገባው ሂደት እንኳን ቀድሞ የሚነሳው ጥያቄ፡ በልማት ስም ከተሰሩት እና ወደፊትም ከሚሰሩት ግፎች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ጥቂት ኮሚቴዎችን ብቻ በጥቅም አስሮና አሳምኖ የአንድን መንደር ነዋሪ በሙሉ ለከፋ ችግር ከመዳረግ፡ ከአሁኑ ተጠያቂነት ያለበት አሳማኝ ስራ ለመስራት ማሰቡ የተሻለ ነው፡፡ ነዋሪዎችን በልማት ስም አፈናቅሎ መልሶ ነገ ወደሚፈርስ ቦታ እያዘዋወሩ እንደተከራይ ማንከራተት ለከፍተኛ ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማህበራዊ ቀውስ እንደሚዳርጋቸው የምር መታሰብ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ ቀደም ‹‹ለልማት›› ተፈናቃዮች የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ) ቤት  ያለ እጣ  ቀድሞ እንዲሰጣቸው የሚደረግበት አሰራር ነበር፡፡ ወደፊትስ ተመዝግበው ቤት የሚጠብቁ ሰዎችን እጣ ከማራዘም፡ በልማት ስም ለሚነሱ ነዋሪዎች እራሱን የቻለ ተጠባባቂ መኖሪያ በመገንባቱ በኩል ምን አይነት እቅድ ተይዞ ይሆን የሚለው ጥያቄ መልስ የሚሻ ነው፡፡
ከቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት ምዝገባ ጋር በተያያዘ እንደ ዋዛ ሊታለፉ የማይገባቸው ጉዳዮችም አሉ፡፡ ወደ አራት መቶ ሺህ (400.000) ሰው ተመዝግቦበታል የሚባለው የቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት አንድ መቶ ሺህ (100.000) ለሚሞሉ ነዋሪዎች እንኳን አልተዳረሰም፡፡ በነዚህ ሁሉ ዓመታት ይህቺን ብቻ ከሆነ ማሳካት የተቻለው፡ በቀጣይ እየታሰበ ያለው ፕሮግራምስ በተባለው ግዜ ለመድረሱ ምን ዋስትና አለው? የቀድሞ ተመዝጋቢዎች ፋይል ጠፋ መባሉ ምንድነው የሚነግረን? በቀጣይ የተመዘገቡ ሰዎችስ ዋስትናቸው ምንድነው? እስኪጣራ እንደ አዲስ መመዝገባቸውስ ቦሃላ የሚጣራበት መንገድ ስለመኖሩ ዋስትና ይሰጣል? ቀድሞ የመመዝገብ እድሉን አግኝተው የነበሩ ነገር ግን አሁን የተባለውን ገንዘብ መቆጠብ የማይችሉ ነዋሪዎች እየገጠሙን ነው፤ የነሱስ ተስፋ ምንድነው?
ከቤት ልማት ጋር በተያያዘ የሚሰሩ መስሪያ ቤቶች ለሙስና የተጋለጡና በተለያየ ግዜም እንደሚቀያየሩ ይታወቃል፤ ታዲያ ህዝቡ አዲሱን ፕሮግራም እንደሚያስፈጽሙ እንዴት እምነት ሊጥልባቸው ይችላል? ከግል ተቋራጮች ጋር ያለው የዋጋ ልዩነትና ቤቱን መረከቢያ የግዜ ምጣኔ መንግስት ካቀረበው ጋር ያለው ልዩነት ተመዛዝኖ ይሆን? ህብረተሰቡ የሚጠይቃቸው ጥያቄዎች ናቸው፡፡
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ባለፈው ቅዳሜ ለአዲስ ጉዳይ መጽሄት (ቅጽ7 ቁጥር 169 ሰኔ 005) በላከው ደብዳቤ ላይ እንደገለጸው ‹‹…ዋናው ጉዳይ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ተነድፏል ወይ? የሚለው  ጥያቄ በአግባቡ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ማረጋገጡ ነው፡፡…›› ይላል፡፡ እኔ ግን ይህንኑ ጥያቄ መልሼ ለራሱ ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መጠየቅ እወዳለው፡፡ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ስለመነደፉ ምን ያህል እርግጠኞች ናችሁ? ዋስትናስ መስተት ይቻላቹሀል? መልሱን ተጨባጭ በሆነ መረጃ ብታሳዩን መልካም ነው፡፡
ይሕው ከላይ የተጠቀሰው ደብዳቤ ‹‹ዓላማችን ከተሞቻችንን የልማት የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ማዕከላት ማድረግ ነው!!›› የሚል መልዕክት በመዝጊያው ላይ አስፍሯል፡፡ እውነት በከተማችን ውስጥ የምናያቸው ከቤት ግንባታና መልሶ ማልማት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ከላይ የተጠቀሱትን የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ዓላማዎች  (ልማት፡ዲሞክራሲና መልካም አስተዳደር) የሚያሟሉ ናቸው? በልማት ሰበብ የተፈናቀሉትን በአግባቡ አለማስፈር፡ በከተማዋ ውስጥ ያለው የቤት ችግር በአግባቡ ካልተቀረፈ፡ በመስሪያ ቤቱና በነዋሪው ዘንድ መግባባትና መተማመን ካልተፈጠረ፡… ከተዘረዘሩት ውስጥ የትኛውን አላማ ለማሳካት  እንደምትጥሩ ማወቁ ያጓጓል፡፡
አንድ ወዳጄ የሰሞኑን የቤት ባለቤትነት ምዝገባ ይፋ መደረግ ተከትሎ  ‹‹ቆጥ ላይ ከማደራችን በፊት ደረሱልን›› ነበር ያለው፡፡ በእርግጥ አሁንም ህብረተሰቡ እንደደረሳችሁለት እርግጠኛ መሆን ይፈልጋል፡፡ እንደኔ እምነት አዲስ አበባ ላይ ማደሪያ ቆጥ እንኳን በአማራጭነት ስለመገኘቱ በእርግጠኝነት መናገር ይከብደኛል፡፡ወዳጄ ግን ከ‹‹ደረሱልን›› ወደ ‹‹ደረሱብን›› ከመሸጋገሩ በፊት  ችግሩን የምር መረዳትና ተጨባጭ መፍትሄ መፈለጉ ለሁላችንም ሳይበጀን አይቀርም፡፡                          

ስጋት የተጫነው የቤት ባለቤትነት ተስፋ


በመሐመድ ሐሰን
አዲስ አበባን ለኑሮ የማትመች ሲኦል ካደረጓት ምክንያቶች ውስጥ አንዱና ዋነኛው ቤት የማግኘት ችግር ነው፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ ገንዘብ ከፍሎ እንኳን ቤት ማግኘት በጣም አታካች ከመሆኑም ባሻገር: ከቤቶቹ ጥራትና ዋጋ ጋር በተያያዘ የሚነሳው ቅሬታም ቢሆን ከኢትዮጵያዊነት ስብዕና የራቀ ግፍ የሚፈጸምበት ነው፡፡ እንዲህ ያለው ቀዳሚና ግዙፍ ችግር መፍትሄ ሊበጅለት ነው ሲባል ደግሞ የህዝቡ በተስፋ መሞላት እና መፈንጠዝ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከሰሞኑ የንግድ ባንኮችን እና ቀበሌዎችን አጨናንቆ የተመለከትነው ሰልፍም የዚሁ ተስፋ ማሳያ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን የከተማዋን ዋነኛ ችግር ለመቅረፍ የተወጠነው እቅድ በጎ ስለመሆኑ ማንኛውም ሰው ይስማማል፡፡ ነገር ግን በተስፋ ከተጨናነቁት ሰልፎች ውስጥም ቢሆን የሚነሱት ስጋቶችና ጥያቄዎች፡ ውሃ የማይቋጥሩ ናቸው በሚል እንደ ቀልድ የሚታለፉ አይደሉም፤ ለተጨማሪ እይታ በር የሚከፍቱ እንጂ፡፡
በፖለቲካ የተጠለፈ ተስፋ?
በ1997 ዓ.ም የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ ቤት)  ምዝገባ ሲካሄድ፡ ጉዳዩን ከፖለቲካ ጋር በማያያዝ ሳይመዘገቡ የቀሩ በርካቶች ነበሩ፡፡ አሁን የተጀመረውን አዲሱ ምዝገባም ቢሆን ከፖለቲካው ጋር ያያዙት ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ጉዳዩን በበላይነት ይዘነዋል የሚሉ የስራ ሃላፊዎችም፡ በሰሞነኛው የቤት ባለቤትነት ጉዳይ ላይ የተለያየ ሀሳብ የሚሰነዝሩ መገናኛ ብዙሀንን፡ የፖለቲከኛ አለቆቻቸውን አፍ በመዋስ ‹‹ተላላኪ›› ሲሉ አድምጠናል፡፡ 
ጉዳዩን ከፖለቲካው ጋር የሚያያይዙት ሰዎች በቀዳሚነት የሚያነሱት ከምርጫ ጋር የተያያዘውን ነጥብ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ፡ ‹‹የዚህች ሀገር ብቸኛው ልማት አብሳሪ እኔ ነኝ፡ እኔ ከሌለው ሀገሪቱ ትበታተናለች፡…›› ከሚለው ልማዳዊ ዲስኩሩ በመነሳት፡ አሁን የሚጀመረውን የቤት ግንባታ ፕሮግራምም ከሱ ውጪ ሌሎች እንደማይጨርሱት ማሳመን ይፈልጋል ሲሉ ይወቅሱታል፡፡ ባለስልጣናቱም ከዚሁ ስጋት ጋር በተያያዘ ለህብረተሰቡ ግልጽ ያለ መረጃ በማቀበል ዋስትና መስጠት የሚፈልጉ አይመስሉም፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ግንባታው ከተያዘለት የግዜ ገደብ በመነሳት፡ ሂደቱን ለቀጣይ ሁለት ምርጫዎች የተከፈለ ቀብድ ነው የሚለውን ሀሳብ አጠንክሮታል፡፡ እንዲህ ያለው የፖለቲካ ጨዋታ ደግሞ ህዝቡን ለተጨማሪ የባርነት እና እስረኛነት ህይወት መዳረጉ እሙን ነው፡፡ ከዚህ ስትራቴጂ በመነሳትም ‹‹ቁሳዊ ሀብትን ብቻ በማብሰር እስከመቼ እያበሉ መግዛት ይቻላል?›› የሚለው ጥያቄ ተያይዞ ይነሳል፡፡
ፓርቲውና ባለስልጣናቱ መሬት ሲቸበችቡ እና ቤት ሲሰሩ በመኖራቸው፡ ህዝቡ ውስጥ ያለውን ብሶት ለማስተንፈስ በሚል የሰሞኑ ተስፋ ሆን ተብሎ እንደተፈጠረ የሚጠረጥሩም አሉ፡፡ ምሁራን እና ተቃዋሚዎችም በጉዳዩ ላይ አማራጮችን በመጠቆም ዋስትና ከመስጠት በመቆጠባቸው ከህዝቡ ትችት አላመለጡም፡፡
ጉዳዩን በበላይነት የሚቆጣጠሩት ሰዎች ከፖለቲካው ነጻ ናቸው ተብሎ ስለማይታመን፡ የፓርቲው አባላት በተለያየ መንገድ ከግናባታው ሂደት ብቸኛ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ሊደረግ የሚችልበት እድልም ሰፊና ብዙዎች የሚጋሩት ስጋት ነው፡፡ ከቀደሙ ተሞክሮዎች በመነሳት መናገር እንደሚቻለው፡ ለስራው የሚያስፈልጉ ግብአቶች በሙሉ በፓርቲው ስር የተደራጁ አባላት እንዲያቀርቡ ይደረጋል፤ ከጥቃቅን የመንገድ ስራዎች ጀምሮ እስከ ቤቶቹ ግንባታ ድረስ ያለው ስራም ለአባላቱ ተመርጦ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ ጉዳዩን ከሀገራዊነት ወደ ፓርቲያዊነት ያወርደዋል፡፡
ያልተመለሱ ጥያቄዎች
ከፖለቲካዊ አንድምታው በበለጠ አዲሱ የቤቶች ልማት ፕሮግራም በርካታ ያልመለሳቸው ውስብስብ ጥያቄዎች ይነሱበታል፡፡ ከሁሉም በላይ ከምዝገባው ሂደት እንኳን ቀድሞ የሚነሳው ጥያቄ፡ በልማት ስም ከተሰሩት እና ወደፊትም ከሚሰሩት ግፎች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ጥቂት ኮሚቴዎችን ብቻ በጥቅም አስሮና አሳምኖ የአንድን መንደር ነዋሪ በሙሉ ለከፋ ችግር ከመዳረግ፡ ከአሁኑ ተጠያቂነት ያለበት አሳማኝ ስራ ለመስራት ማሰቡ የተሻለ ነው፡፡ ነዋሪዎችን በልማት ስም አፈናቅሎ መልሶ ነገ ወደሚፈርስ ቦታ እያዘዋወሩ እንደተከራይ ማንከራተት ለከፍተኛ ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማህበራዊ ቀውስ እንደሚዳርጋቸው የምር መታሰብ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ ቀደም ‹‹ለልማት›› ተፈናቃዮች የኮንዶሚኒየም (የጋራ መኖሪያ) ቤት  ያለ እጣ  ቀድሞ እንዲሰጣቸው የሚደረግበት አሰራር ነበር፡፡ ወደፊትስ ተመዝግበው ቤት የሚጠብቁ ሰዎችን እጣ ከማራዘም፡ በልማት ስም ለሚነሱ ነዋሪዎች እራሱን የቻለ ተጠባባቂ መኖሪያ በመገንባቱ በኩል ምን አይነት እቅድ ተይዞ ይሆን የሚለው ጥያቄ መልስ የሚሻ ነው፡፡
ከቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት ምዝገባ ጋር በተያያዘ እንደ ዋዛ ሊታለፉ የማይገባቸው ጉዳዮችም አሉ፡፡ ወደ አራት መቶ ሺህ (400.000) ሰው ተመዝግቦበታል የሚባለው የቀድሞው የጋራ መኖሪያ ቤት አንድ መቶ ሺህ (100.000) ለሚሞሉ ነዋሪዎች እንኳን አልተዳረሰም፡፡ በነዚህ ሁሉ ዓመታት ይህቺን ብቻ ከሆነ ማሳካት የተቻለው፡ በቀጣይ እየታሰበ ያለው ፕሮግራምስ በተባለው ግዜ ለመድረሱ ምን ዋስትና አለው? የቀድሞ ተመዝጋቢዎች ፋይል ጠፋ መባሉ ምንድነው የሚነግረን? በቀጣይ የተመዘገቡ ሰዎችስ ዋስትናቸው ምንድነው? እስኪጣራ እንደ አዲስ መመዝገባቸውስ ቦሃላ የሚጣራበት መንገድ ስለመኖሩ ዋስትና ይሰጣል? ቀድሞ የመመዝገብ እድሉን አግኝተው የነበሩ ነገር ግን አሁን የተባለውን ገንዘብ መቆጠብ የማይችሉ ነዋሪዎች እየገጠሙን ነው፤ የነሱስ ተስፋ ምንድነው?
ከቤት ልማት ጋር በተያያዘ የሚሰሩ መስሪያ ቤቶች ለሙስና የተጋለጡና በተለያየ ግዜም እንደሚቀያየሩ ይታወቃል፤ ታዲያ ህዝቡ አዲሱን ፕሮግራም እንደሚያስፈጽሙ እንዴት እምነት ሊጥልባቸው ይችላል? ከግል ተቋራጮች ጋር ያለው የዋጋ ልዩነትና ቤቱን መረከቢያ የግዜ ምጣኔ መንግስት ካቀረበው ጋር ያለው ልዩነት ተመዛዝኖ ይሆን? ህብረተሰቡ የሚጠይቃቸው ጥያቄዎች ናቸው፡፡
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ባለፈው ቅዳሜ ለአዲስ ጉዳይ መጽሄት (ቅጽ7 ቁጥር 169 ሰኔ 005) በላከው ደብዳቤ ላይ እንደገለጸው ‹‹…ዋናው ጉዳይ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ተነድፏል ወይ? የሚለው  ጥያቄ በአግባቡ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ማረጋገጡ ነው፡፡…›› ይላል፡፡ እኔ ግን ይህንኑ ጥያቄ መልሼ ለራሱ ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መጠየቅ እወዳለው፡፡ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የሚሆን የቤት አቅርቦት አማራጭ ወይም ስልት ስለመነደፉ ምን ያህል እርግጠኞች ናችሁ? ዋስትናስ መስተት ይቻላቹሀል? መልሱን ተጨባጭ በሆነ መረጃ ብታሳዩን መልካም ነው፡፡
ይሕው ከላይ የተጠቀሰው ደብዳቤ ‹‹ዓላማችን ከተሞቻችንን የልማት የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ማዕከላት ማድረግ ነው!!›› የሚል መልዕክት በመዝጊያው ላይ አስፍሯል፡፡ እውነት በከተማችን ውስጥ የምናያቸው ከቤት ግንባታና መልሶ ማልማት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ከላይ የተጠቀሱትን የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ዓላማዎች  (ልማት፡ዲሞክራሲና መልካም አስተዳደር) የሚያሟሉ ናቸው? በልማት ሰበብ የተፈናቀሉትን በአግባቡ አለማስፈር፡ በከተማዋ ውስጥ ያለው የቤት ችግር በአግባቡ ካልተቀረፈ፡ በመስሪያ ቤቱና በነዋሪው ዘንድ መግባባትና መተማመን ካልተፈጠረ፡… ከተዘረዘሩት ውስጥ የትኛውን አላማ ለማሳካት  እንደምትጥሩ ማወቁ ያጓጓል፡፡
አንድ ወዳጄ የሰሞኑን የቤት ባለቤትነት ምዝገባ ይፋ መደረግ ተከትሎ  ‹‹ቆጥ ላይ ከማደራችን በፊት ደረሱልን›› ነበር ያለው፡፡ በእርግጥ አሁንም ህብረተሰቡ እንደደረሳችሁለት እርግጠኛ መሆን ይፈልጋል፡፡ እንደኔ እምነት አዲስ አበባ ላይ ማደሪያ ቆጥ እንኳን በአማራጭነት ስለመገኘቱ በእርግጠኝነት መናገር ይከብደኛል፡፡ወዳጄ ግን ከ‹‹ደረሱልን›› ወደ ‹‹ደረሱብን›› ከመሸጋገሩ በፊት  ችግሩን የምር መረዳትና ተጨባጭ መፍትሄ መፈለጉ ለሁላችንም ሳይበጀን አይቀርም፡፡