Friday, October 25, 2013

ኢህአዴግ እዳ አለበት! ፫


ርዕዮታዊው መንፈስ እንደ ‹‹ቻይኒዝ ባምቡ›› ፪
በመሐመድ ሐሰን       (ኢትዮ-ምህዳር ላይ የወጣ)

እኔ እዚህ ብዕሬን ተጠቅሜ ርዕዮታዊውን መንፈስ መመርመሬን ስንቀጥል፣ በሌላ በኩል ደግሞ የኢህአዴግ ባለስልጣናት እና በቃሊቲ ያስቀመጧቸው ቅጥረኞቻቸው የሀገሪቱን ህግ ያለአግባብ በመጠቀም፣ ርዕዮትን (ቤተሰቦቿን) መወንጀላቸውን እና ማሰቃየታቸውን አጠናክረው ገፍተውበታል፡፡ እንግዲህ ‹‹ከሳሽ ዳኛ ሆኖ…›› ማለት ይሄኔ ነው፡፡ ቀድሞ በተጠነሰሰ ሴራ ከሰሞኑ በመገናኛ ብዙሀኑ ስንሰማ እንደነበረው፣ የሚፈልጉትን እርምጃ ወስደው በወዳጅ ዘመድ እንዳትጠየቅ ካደረጓት ቦሃላም ቢሆን የበቀል ግልቢያቸውን አላቆሙም፡፡  ማንም ሰው እንዳያወራት አድርገዋል፤ የህግ መሰረት የሌለውን ትዕዛዝ አልቀበልም ብላ እያወራቻት እና አጋርነቷን እያሳየቻት የነበረችውን፣ ሌላኛዋን ጠንካራ ሴት ፈትያ መሐመድን ከርዕዮት ነጥለው ሌላ ቦታ አዛውረዋታል፤ ከሷ ጋር መልዕክት ይለዋወጣሉ ብለው የጠረጠሯቸውን እጅግ በጣም አሳፋሪ በሆነ መልኩ የማሸማቀቅ ተግባር እየፈጸሙባቸው ነው፤…ሌላም ሌላም በርካታ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶች እየተፈጸሙ ያሉት ህግ አለ በሚባልበት ቃሊቲ ግቢ ውስጥ ነው፡፡
በተለይ ርዕዮት ዓለም አቀፍ ሽልማቶችን ስታገኝ እና ስትታጭ፣ ወንጀላቸውን በመላው ዓለም ይበልጥ ስለሚያስተጋባው፣ እርምጃቸውን ጠንከር ያደርጉታል፡፡ ከሰሞኑ የሚወስዱት እርምጃዎች የጠበቀበት አንዱ ምክንያትም ይሄው ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ርዕዮት ለ2013ቱ የሳካሮቭ ሽልማት ታጭታለች፡፡ ዓለምዓቀፍ እውቅናው ላቅ ያለው ይህ ሽልማት ለሐሳብ ነጻነት ለታገሉና ለሚታገሉ የሚሰጥ የአውሮፓ ፓርላማ የዓመታዊ ክንዋኔው አንድ አካል ሲሆን፣ ዘንድሮ ለመጨረሻው ሽልማት ከቀረቡ ሰባት እጩዎች ውስጥ ሁለቱ ኢትዮጵያውያን እስክንድር ነጋ እና ርዕዮት ዓለሙ ናቸው፡፡ ሁለቱም በቃሊቲው መንግስት ስቃይ ስር ቢሆኑም፣ ዓለም ግን በጀግንነታቸው ሊሸልማቸው አጭቷቸዋል፡፡       
እንግዲህ መካሪ ያጣው ኢህአዴግ ኪሎው የሚወርድብን ይሄኔ ነው፡፡ ማንንም ማሸነፍ በማይችልበት ደረጃ መሽመድመዱን ማሳያ ነች በእድሜ ትንሿ ርዕዮት፡፡ ‹‹የሞኝ ለቅሶ…›› እንዲሉ ከዚህ በፊት ከዚህ በከፋ መልኩ ሞክረው ያልተሳካላቸውን ሙከራ ነው በከንቱ እየተገበሩት ያሉት፡፡ አሁን ርዕዮት ላይ እየተወሰዱ ያሉት እርምጃዎች ዋነኛ ዓላማ የመንፈስ ጥንካሬዋን (ርዕዮታዊውን መንፈስ) ለመንጠቅ ነው፡፡ ግን አልቻሉም፤ አይችሉምም! ምክንያቱም በባለፈው ጽሁፌ ላይ በተወሰነ መልኩ ለመግለጽ እንደሞከርኩትና ቦሃላም በደንብ እንደምገልጸው፣ ርዕዮታዊው መንፈስ ዝም ብሎ በእስሯ የመጣና በቀላሉ የሚከሽፍ አይደለም፡፡ ለማንኛውም እነሱ የተካኑበትን የህገ ወጥነት ተግባር ይቀጥሉበት፣ እኔ ደግሞ የርዕዮታዊውን መንፈስ ምርመራ በመቀጠል ዓላማቸው እንዴት እንደማይሳካ ለማሳየት እሞክራለው፡፡
ርዕዮት ለምን ታሰረች?
ባለፈው ሳምንት ጽሁፌ ላይ ለመጠቃቀስ እንደሞከርኩት የርዕዮት እስር ምንም ዓይነት ህጋዊ መሰረት የሌለው፣ እንዲሁም የፍርድ ሒደቱ አንዳችም ተጨባጭ ማስረጃ ያልቀረበበት እና  ቀሽም ፖለቲከኞች የደረሱት ፖለቲካዊ ድራማ ነበር፡፡ ከዚህ ቦሃላ ወደ አንባቢዎች ህሊና ሊመጣ የሚችለው አንደኛው ጥያቄ ‹‹እና ታዲያ ለምን ታሰረች?›› የሚል ሊሆን ይችላል፡፡ ለዚህ ጥያቄ አይደለም እኔ አሳሪዎቿ እንኳን ቁርጥ ያለ አንድና ብቸኛ መልስ የላቸውም፡፡ አረ እንደውም ጭራሽ መልስ የላቸውም! ብቻ አንድ ዕለት የኢህአዴግ ካድሬዎች ከእንቅልፋቸው ሲነቁ፣ ርዕዮት የምትባል በሳል ጋዜጠኛ ውል አለችባቸው፡፡ ከዛ ቦሃላ የተወሰኑ ግብዞች ይነሳሱና ከምታስተምርበት መንግስታዊ ትምህርት ቤት ስብሰባ ጨርሳ ስትወጣ አፈፍ አድርገው ከመኪናቸው ላይ ዶሏት፡፡
በወቅቱ ርዕዮት እውነታው (የነሱ እውነት) እስኪገለጥላት ሊፍት ያገኘች ሳይመስላት እንዳልቀረ እገምታለው፡፡ እውነታቸው ሲገለጥላት ርዕዮት ከመደንገጥ ይልቅ መገረሟ ቅድሚያ እንደሚኖረውም እጠረጥራለው፡፡ ከወዳጇቿ እና ከቤተሰቧ ውጪ ሌላ ሰው ያውቀኛል ብላ ያልገመተችው ርዕዮት፣ ለካ ኢህአዴጋውያኑ ክፉ ቀልባቸው አርፎባት ኖሯል፡፡ እሷም የታሰረች ሰሞን ‹‹ኢህአዴግ መውረዱ የገባኝ እኔ ጋር ሲደርስ ነው?›› ዓይነት ንግግሯን ሹክ ብላናለች፡፡ እዚህች ጋ ‹‹ኢህአዴግ ወርዶ ወርዶ…›› ዓይነት ማጀቢያ ሙዚቃ ብንሞዝቅ አሪፍ ሳሆን አይቀርም፡፡ ለማነኛውም እኔ ለርዕዮት እስር ምክንያት ናቸው ያልኳቸውን ነጥቦች ልዘርዝር፡፡
አንደኛ፡- የርዕዮት እስር አሳሪዎቿ (የኢህአዴግ ባለስልጣናት) ለግለሰብ ያላቸውን ፍራቻ እና ከግለሰቦች ጋር የተጋቧቸው እልሆች ማሳያ ነው፡፡ ብዙ ነገሮችን ማስተዋል ከቻልን፣ መሪዎቻችን ሀገሪቱን የሚጎዱ በርካታ ውሳኔዎችን ከግለሰቦች ጋር ካላቸው ግንኙነት በመነሳት ውሳኔ ያሳልፋሉ፡፡ በዚህ መንገድ ካየነው፣ የርዕዮት እስር ለዳያስፖራ ፖለቲከኞች (ተቀናቃኞቻቸው) ያላቸውን ፍራቻ አልያም ጥላቻ የምንመለከትበት ነው፡፡ ምክንያቱም ርዕዮት የኢትዮጵያን መንግስት አቋም አጥብቆ ለሚተቸው ኢትዮጵያንሪቪው (ethiopianreview) ድረ-ገጽ በሪፖርተርነት መስራት እንደጀመረች ነው ብዙም ሳይቆይ ለእስር የተዳረገችው፡፡
ከታሰረች ቦሃላ በፍርድ ቤት የነበረው ሂደት ላይም እንደተከታተልነው፣ የከሳሾቹ ዋነኛ ትኩረት የነበረው ኤልያስ ክፍሌ የተባለው የ ethiopianreview ድረ-ገጽ ባለቤት ነው፡፡ ይህንን ሰው ደግሞ ደጋግመው ከነ ግንቦት ሰባት እና መሰል አካላት ጋር እያያያዙ ያነሱታል፡፡ ርዕዮትን ደግሞ ‹‹ከዚህ ሰው የሽብር ተልዕኮ ስትቀበይ ነበር›› ይሏታል፡፡ ምን ዓይነት ተልዕኮ እንደተቀበለች ግን አንድም ማስረጃ አላቀረቡም፡፡ እውነታውን ማወቅ ስለማይሹ እንጂ፣ ርዕዮት በጽሁፏ ጭምር የሰላማዊ ትግል አቀንቃኝነቷን በተደጋጋሚ ከመግለጽ ባለፈ በተቃራኒው የቆሙትንም ደህና አድርጋ መሸነንቆጥ ችላለች፡፡
የሷን ጉዳይ እንኳን ትተን ኤልያስ በሚሉት ሰው ላይ እንኳን ሲያቀርቡት የነበረው ማስረጃ በግልጽ ለ ኢሳት ቴሌቪዥን ጣቢያ የሰጠውን ቃለ-ምልልስ ነበር፡፡ ልብ ማለት የሚገባው ሌላኛው ጉዳይ እነ ርዕዮት ዋነኛ ጥፋታቸው ተደርጎ የቀረበው ከኤልያስ ጋር መገናኘታቸው ሲሆን፣ እስከዚህ ግዜ ድረስ ግን ኤልያስም ሆነ ethiopianreview በሽብርተኝነት አልተፈረጁም፤ በፍርድ ቤት የተላለፈባቸው ውሳኔም አልነበረም፡፡
እንግዲህ እንዲህ ባለው ሁኔታ ርዕዮት ለድረ-ገጹ በሪፖርተርነት እንደምትሰራ ደጋግማ አረጋገጠች፡፡ እነሱ ግን እውነታውን ሳይሆን ያሰቡትን ብቻ ነበር የሚናገሩት፡፡ በየክፍለሃገሩ መሰረተ ልማቶች ላይ ሊደረግ ለታሰበው ጥቃት እየተሰናዱ ካሉት ውስጥ አንዷ እንደሆነች እና ስልጠናም እንደወሰደች ከሳሾቿ ወተወቱ፡፡ አይደርስ የለ ‹‹ማስረጃ›› የሚሰማበት ቀን ደረሰና ‹‹ማረጃችሁን›› ተባሉ፡፡ ያቀረቡት ማስረጃ ምን መሰላችሁ? ከኤልያስ ክፍሌ ጋር ያደረገችው የስልክ ልውውጥ፡፡ በስልኩ ያስተላለፈላት መልዕክት ምን ነበር? ‹‹አዲስ አበባ ውስጥ የተለያዩ ቦታዎች ላይ ‹‹መለስ በቃ›› የሚል ጽሁፍ ተለጥፏልና ፎቶ አንስተሸ ላኪልኝ›› ይላታል፡፡ የስልክ ልውውጣቸው እነሱ በፈለጉት መልኩ ተቆራርጦ ቢቀርብም፣ በንግግራቸው ወቅት በግልጽ እንደሰማነው፣ ርዕዮት ተጽፏል ያላት ቃልም ሆነ ተጽፎባቸዋል የተባሉት ቦታዎችን ስላላወቀቻቸው ደጋግማ ስትጠይቀው ነበር የሰማነው፡፡…
በመጨረሻም ግን አቃቤ ህጉ የደረደራቸውን አብዛኞቹ ክሶች ‹‹ዳኞቹ›› ውድቅ ቢያደርጉትም፣ ‹‹በቃ›› በሚለው ጽሁፍ ግን ተጠያቂ መሆኗን በመግለጽ ነበር የፈረዱባት፡፡ ሲፈርዱ ምን አሉ፣ ከሰማነው ድምጽ ጋር አብሮ የማይሄድ ‹‹…ጽሁፉ ሲጻፍ እየተከተልሽ ፎቶ ታነሺና መረጃ ታቀብዪ ነበር…›› ሲሉ ጥፋተኛ አደረጓት፡፡ ይህ ሁሉ ድራማ ነው፤ እውነታው የእሷ ከኤሊያስ ጋር ማውራት ስለበርካታ ‹‹ባላንጣዎቻቸው›› በማሰብ የበቀል እርምጃ እንዲወስዱ አድርጓቸዋል፡፡ እንጂማ እንደተላለፈው ውሳኔስ ቢሆን ግድግዳ ላይ የተጻፈን ጽሁፍ ፎቶ ማንሳት አይደለም ለጋዜጠኛ፣ ለሌላውስ ማን ነው የከለከለው? ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ለዚህ መሰል ጥያቄ እነሱ መልስ የላቸውም፡፡
ከዚሁ ነጥብ ጋር በተያያዘ አንድ ነገር ላክል፡፡ ርዕዮት ጉዳይዋ ገና በፍርድ ቤት ታይቶ ሳያልቅ፣ በኤልያስ ላይ መስክራ እንድትወጣ እድል ሰጥተዋት ነበር፡፡ ይህ በአንድ በኩል ጉዳያቸው ከኤልያስ ጋር መሆኑን ሲያሳየን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የርዕዮታዊውን መንፈስ ማንነት በደንብ ይነግረናል፡፡ ኤልያስ የሚኖረው አሜሪካን ሀገር ነው፤ ርዕዮት እና ኢህአዴግ ደግሞ ያሉት እዚሁ ኢትዮጵያ፤ ርዕዮት መስክራበት ልትወጣ ትችል ነበር፤ ከየትም አምጥተው አያስሩትም፤ ትውውቃቸውም ቢሆን ከ ሶስት እና አራት ወራት በላይ ያልዘለቀና እሱም ቢሆን የስራና የስራ ብቻ ነበር፡፡ ለርዕዮት ግን ቁም ነገሩ እሱ አይደለም፤ እውነት ነው፡፡ የማታውቀውን፣ የማታምንበትን፣…ነገር ከማድረግ ልቅ፣ አሁን ያለችበትን መራራ! ጽዋ መቀበልን ትመርጣለች፡፡                     
ሁለተኛ፡- የርዕዮት እስር ለካድሬዎቹ ግላዊ ጥቅም መረማመጃነት ውሏል፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነን በሷም በእጮኛዋም በኩል ወዳጅ መስለው ይቀርቧቸው የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ የእነዚህን ሰዎች ስም አሁን ላይ ማንሳት ተገቢ ባይሆንም፣ በደንብ የሚያውቁትን እውነታ አንሻፈው በማቀበል ፣ከፓርቲያቸው ተጨማሪ ሹመት ለማግኘት ሲሉ እነ ርዕዮትን በመስዋዕትነት አቅርበዋቸዋል፡፡     
ሶስተኛ፡- የርዕዮት እስር በስህተት የተፈጸመ ነው ለማለት የሚያስችሉ ምክንያቶችም አሉ፡፡ ካድሬዎቹ እና ባለስልጣናቱ ርዕዮትን ተረባርበው ካስያዟት ቦሃላ፣ የተወሰኑ መርማሪዎቿ ጋር የነበረው መረጃ ፍጹም የተሳሳተ ነበር፡፡ በመጀመሪያ የተያዘች ሰሞን ‹‹ኤርትራ ድረስ በመሄድ የአሰልጣኝነት ስልጠና ወስዳለች…›› የሚል የ‹‹በሬ ወለደ›› ክስ ቀርቦባት ስለነበር፣ ለበርካታ ግዜ መርማሪዎቿ ጋር ስትቀርብ እጇን በሰንሰለት ታስራ ነው፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ወሰደች ባሉት ስልጠና እንዳትዘርራቸው በመፍራት ነበር፡፡ ታዲያ እውነታው የተገለጸላቸው አንድ ቀን እንደታሰረች የታሸገ ዉሃ መክፈት ሲሳናት በማየታቸው ነበር፡፡ ይሄኔ መንግስትም መርማሪዎችም በቀሽም ካድሬዎቻቸው እንደተሸወዱ መጠርጠር ስህተት አይሆንም፡፡      
አራተኛ፡- የርዕዮት እስር ከስራዋ ጥንካሬ የመጣ እንደሆነም መገመት ይቻላል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ብዙ ግዜ ፕሬሶች ላይ የሚወስደው እርምጃ ከጥንካሬያቸው ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሀሳብ አላቸው ብሎ የሚያስባቸው ፕሬሶች እና ጋዜጠኞች ላይ በተለያየ መንገድ ጠንከር ያሉ እርምጃን የሚወስድ ሲሆን፣ ብዙም የማያሰጉትን ግን በተለሳለሱ አካሄዶች ያዝ ለቀቅ እያደረገ ያንገዳግዳቸዋል፡፡ የርዕዮትን ስራዎች በምናይበት ግዜም፣ ጽሁፎቿ ሀሳብ ያላቸው እና በጠንካራ ምክንያታዊነት ላይ የተመሰረቱ ናቸው፡፡ ለዚህም ማሳያው ከጽሁፎቿ ጋር በተያያዘ (በተለይ ‹‹አዲስ ፕሬስ›› ጋዜጣ ላይ ስትሰራ) በየግዜው ከመንግስት አካላትም ጭምር ምላሾች እየመጡ በጋዜጣው ላይ ወጥተዋል፡፡ በግልም ቢሆን ስልኮች የሚደወሉላት ሲሆን፣ ከተለያዩ ቦታዎች ዛቻና ስድብ ያዘሉ በርካታ ገጽ ያላቸው ደብዳቤዎች ደርሰዋት ያውቃሉ፡፡ ነገር ግን ፋይዳ ስላልነበራቸው ለፍጆታነት አውላቸው አታውቅም፡፡            
ስለዚህ በየትኛውም መንገድ ብንሄድ የርዕዮት እስር ምንም ዓይነት ህጋዊ መሰረት የሌለው ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ‹‹እና ታዲያ ለምን አየረፈቷትም?›› የሚለው የበርካቶች ጥያቄ የሚመጣው ይህንን ተከትሎ ነው፡፡ አርግጥ ነው መንግስት ርዕዮትን ሊፈታት የፈለገው ቀደም ብሎ ነው፡፡ ነገር ግን ርዕዮትን መፍታት የእስሩን ያህል ቀላል አልነበረም፡፡ እንደፈለጉት ልትንበረከክላቸው አልቻለችም፤ የሀሰት ምስክርነቱንም አላገኙም፡፡ ይህን ማድረግ ባለመቻላቸው እና የበላይነቱን ስለነጠቀቻቸውም ጭምር ነው ሰሞነኛውን ኢህአዴጋዊ አጉል መንፈራገጥ እያስተዋልን ያለነው፡፡ ነገር ግን የሚቻላቸው አይደለም፤ ምክንያቱም የርዕዮታዊው መንፈስ ጥንካሬ እስከ አሁን ድረስ ሊገባቸው አልቻለም፡፡
የርዕዮታዊው መንፈስ ጥንካሬ ማሳያዎች እና ፈተናዎቹ
በቀደሙት ጽሁፎቼ ላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት የርዕዮት ጥንካሬ መሰረት ያለው እና በሁኔታዎች መመቸት እና አለመመቸት የሚቀያየር አይደለም፡፡ ጥንካሬው እና እምነቱ የሚጀምረው ከቤት ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ብዙ ምሳሌዎችን ማንሳት ቢቻልም፣ ከቅርቡ አንድ ብቻ ልጥቀስ፡፡  አሁን ማንም እንዳይጠይቃት በተከለከለችበት እና አባቷ እና እናቷ ብቻ ጠያቂ እንዲሆኑ ሲፈቀድላቸው አባቷ የሰጡት ምላሽ በምን አይነት የሞራል ክበብ ውስጥ እንዳደገች አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ‹‹ሌላ ሰው እየተከለከለ እኔ እንዴት እገባለው? ይህ ህገወጥነት ነው፤ ከህገ ወጦች ጋር ደግሞ አልተባበርም!›› ነው ያሉት፡፡ ይህ ውሳኔ እንዴት ያለ ክብደት እንዳለው ለማወቅ የግድ አባት ሆኖ ማየትን የሚጠይቅ አይመስለኝም፡፡
ከዚህ ባለፈ ርዕዮት ከንባብ እና በዙሪያዋ ካሉ ሰዎች ያገኘችው እውቀት የማንነቷ መሰረቶች ሲሆኑ፣ ‹‹አማን›› የተሰኘው የምክክር ቡድናቸው ደግሞ ከጥንካሬዋ ጋር ብቻ ሳይሆን፣ መንፈሱን በመጋራት በኩልም ቢሆን ቀዳሚው ነው፡፡ ሌላው ርዕዮት በእስር ላይ እንኳን እያለች ለአደባባይ ማብቃት የቻለቻቸው ጥቂት ጽሁፎቿ የአቋም ለውጥ የማይታይባቸው እና የጥንካሬዋ ማሳያዎች ናቸው፡፡
አስታውሳለው ከርዕዮት ጋር ከፍተኛ ሙግት ካደረግንባቸው ግዚያቶች አንዱ የ‹‹አዲስ ነገር›› ባልደረቦች ሀገር ለቀው የወጡበት ወቅት ነበር፡፡ በዛን ግዜ ርዕዮት በፍጹም መውጣት እንዳልነበረባቸው አጥብቃ ሞገተችኝ፡፡ እኔ ደግሞ የራሳቸው ዓላማ እና አሳማኝ ምክንያት ቢኖራቸው ነው ዓይነት ሙግት አነሳው፡፡ የሆነው ሆኖ አዲስ ነገሮች ከሀገር ከወጡ ቦሃላ ባልጠበቅነው መልኩ ከመጥፋታቸው ባለፈ አንዳንዶቹ መውጣት እንዳልነበረባቸው ሲገልጹ (ለምሳሌ ታምራት ነገራ ‹‹ነብር ዥንጉርጉርነቱን ኢትዮጵያዊ ክሽፈቱን…›› በተሰኘው ጽሁፉ ላይ ገልጾታል፤) ወዲያው የርዕዮት ሙግት ነበር ትዝ ያለኝ፡፡ ርዕዮት ይህን ውጪ የነበረው አቋሟ ዛሬ እስር ቤት በመሆኗ አልተለወጠም፡፡   
ርዕዮት እስከ አሁን የጠቀስኳቸው እና ሌሎችም የጥንካሬዋ ማሳያዎች በተደጋጋሚ አደገኛ ፈተናዎች ገጥሟቸዋል፡፡ ፈተናዎቹ ከአሳሪዎቿ እና ከራሷ ወገን ጭምር የመጡ ቢሆኑም፣ እሷ ግን በብቃት አልፋቸዋለች፡፡ ከአቋሟም ንቅንቅ ሊያደርጓት አልቻሉም፡፡ በማዕከላዊ 13 ቀን  ምግብ ከልክለው ለብቻዋ ጨለማ ክፍል ውስጥ አስረው ከማሰቃየት ጀምሮ ምትወደው እጮኛዋን አስሮ  እስከማሰቃየት ተደጋጋሚ በደል ተፈጽሞባታል፡፡ ርዕዮት ግን ከዚህም በላይ ህይወቷን መስጠት ካለባት በፍጹም ወደ ኋላ የማትል መንፈሰ ጠንካራ እና ለዓላማዋ ስትል ሟች ናት፡፡
ሐላፊነት ካለመውሰድ ጋር በተያያዘ ርዕዮት በዙሪያዋ ባሉ ሰዎች እንኳን ተከድታ እምነቷ ቅንጣት ታህል አልተሸራረፈም፡፡ ከርዕዮት በተጨማሪ ቤተሰቧ እና እጮኛዋ የርዕዮትን መታሰር ተከትሎ በብዙ ወዳጆቻቸው ተከድተዋል፡፡ በተቃውሞ ፖለቲካ ውስጥ ያሉ የቅርብ ዘመዷ እንኳን ሳይቀሩ ርዕትን ለመጠየቅ አይደፍሩም፡፡ በችግራቸው ግዜ ይደርሱላቸው የነበሩ ወዳጆቻቸው ከእስሯ ቦሃላ ሸሿቸው፡፡ በስራው ዓለም የረዳቻቸው ሳይቀሩ ከሷ ጋር ለተያያዙ ጉደዮች ቸልተኛ ሆኑ፡፡ እጮኛዋን ጨምሮ እህቷም የስራ ዋስትናቸውን አጡ፡፡… ሰማይ ምድሩ እስኪጨልምባቸው ድረስ ለከፍተኛ ችግር ተዳረጉ፡፡ ሆኖም ግን እነዚህ ሁሉ ስቃዮች አሁንም የርዕዮትን አቋም እና እምነት የሚያስቀይሩ አልነበሩም፡፡ ዓላማዋ እሰከ መቃብርም ድረስ አብሯት የሚወርድ ለመሆኑ እሷም ጭምር አስረግጣ ትናገራለች፡፡ ሞት ለርዕዮት አስፈሪ ነገር እንዳልሆነ የሚያውቋት ሁሉ የሚያውቁት ሀቅ ነው፡፡ ይህን ዓላማዋን እንደማትቀይር ስትናገር፣‹‹ርዕዮት የአቋም ለውጥ ታደርጋለች ብላችሁ ስጋት አይግባችሁ!›› ትላለች፡፡ ከእስር ቤት ውጪ ያለነውንም ቢሆን ነጻ ነን ብላ አታስብም፤ ለዚህም ነው ‹‹በርቺ›› ስንላት፣ ‹‹እናንተም በርቱ፤ በዘጠነኛው ዞን ውስጥ ነውና ያላችሁት፡፡›› የሚል ምላሽ ነበር የምትሰጠን፡፡
ታዲያ ይህ ርዕዮታዊው መንፈስ አሳሪዎቿ እንዳሰቡት የማይረታ ከመሆኑ ባለፈም፣ የራሱን ተከታዮች እና የመንፈሱ ተቋዳሾችን ማፍራቱ አልቀረም፡፡ ወደፊትም እውነት ቦታዋን ስትይዝ የበላይነቱን እንደያዘ ይበልጥ ይጎመራል፡፡ እስከዛው ድረስ ግን የእውነት ቦታዋ ቃሊቲ ይሆናል፡፡ ሀገሪቱም ምንም ባልሰሩ እና ብዙ ባወሩ እራሳቸውን የዘመኑ ታጋይ እያደረጉ በሚያቀርቡ ትምክህተኞች እንደተወረረች ትቆያለች፡፡ ይህ ነው የአሁኗ ኢትዮጵያ እውነት፡፡ ኢህአዴግም እስከዛው መቼም ከፍሎ የማይጨርሳቸውን ግፎች በመቀፍቀፍ ባለ እዳነቱን አጠናክሮ ይቀጥልበታል፡፡
ለዛሬ የመረጥኳት ግጥም የሰለሞን ሞገስ (ፋሲል) ናት፤ ‹‹እውነትን ስቀሏት!›› ከተሰኘው ድንቅ የግጥም መድብሉ ውስጥ ያገኘኋት ናት፡፡ ርእሷ‹‹ስንቅ የሚያቀብሉኝ እስረኞቹ ናቸው›› ትላለች፤ ይህቺን ግጥም ዶክተር ዳኛቸው በመጽሀፍ ምርቃቷ ወቅት አሪፍ አድርጎ እንደተነተነው አስታውሳለው፡፡ በሱው እንሰነባበት፡፡ በነገራችን ላይ ርዕዮት የማንበብ መብቷን ጭምር የተነፈገች እስረኛ ናት፡፡             

ስንቅ የሚያቀብሉኝ እስረኞቹ ናቸው
እስረኛ ነኝ እኔ መብቱ የጎደለ፣
ነጻ እርግብ ለመሆን ከቶም ያልታደለ፡፡
በአጥር- በጠመንጃ- በዘብ ተጠብቄ፣
በአንዲት ጠባብ ክፍል ምኞቴን አምቄ፣
ታስሬ እኖራለሁ፣
በመጽሀፍ ቅጠል ዓለምን እያየሁ፡፡
የለም ነጻ ሰው ነኝ! እስረኛ አይደለሁም!
ጭንቅና ሰቀቀን ከእኔ ጋራ የሉም፡፡
‹‹እታሰር ይሆን ወይ?›› ብዬ መች ልፈራ?
ታስሬያለሁና ከራሴ እውነት ጋራ፡፡
የሚዳቋ ስጋት፣ ጭንቅ የሞላባቸው፣
የታሰሩትማ በደጅ ያሉ ናቸው፡፡
እኔ ነጻ ሰው ነኝ!
ያሻኝን ሰርቼ፣
የልቤን አውርቼ፤
ይኽው እዚህ አለሁ ነጻነት አግኝቼ፡፡
የታሰሩትማ በውጭ ያሉ ናቸው!
የልብን ለማውራት-
የልብን ለመስራት ወኔ የከዳቸው፣
የሚደናበሩ በገዛ ጥላቸው፣
እኔ ነጻ ሰው ነኝ! የታሰሩትማ ያልታሰሩት ናቸው፡፡ 

ቃሊቲ ደርሶ መልስ ፪


በመሐመድ ሐሰን   (ኢትዮ-ምህዳር ላይ የወጣ)



ትመጪ እንደው እያልኩ ሌት ተቀን ናፋቂ
ሰርክ የማይታክተኝ አለሁሽ ጠባቂ፤
ፍቅር ተደግፌ ቃልኪዳን ታቅፌ
ትመጪ እንደው እያልኩ
ክፍት ነው ደጃፌ፤
አትቀርም እላለው በመላ በጥበብ
ምን ቀን እየገፋ አድሜዬን ብታለል፣
ቆፈን ቢገርፈኝም ጥበቃዬ በዝቶ
እኔ ግን እዛው ነኝ አላጎደልኩ ከቶ፤
ትመጪ እንደው፣
አለሁ እኔ
በፍቅር እንዳለው፡፡ …

እነዚህ ስንኞች የተወሰዱት ‹‹ትመጪ አንደው›› ከሚለው የሚካኤል በላይነህ ሙዚቃ ውስጥ ነው:: እኔ ይህንን ሙዚቃ ስሰማ ከገጣሚው ቴዎድሮ ፀጋዬ፣ ከዜማ ደራሲውና ከዘፋኙ ሚካኤል በላይነህ፣ እንዲሁም ከአቀናባሪው ሚካኤል ሀይሉ ቀድሞ ወደ ህሊናዬ የሚመጣው ጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ ነው:: ዘፈኑ በወጣበት ቀን ስለሺ ስልክ ደውሎ ‹‹ቴዎድሮስ ፀጋዬን አመሰግንልኝ…›› ነበር ይለኝ:: በእርግጥም ስለሺን በቅርበት የሚያውቁት ሁሉ ይህ ግጥም በልኩ ስለመስፋቱ አስረግጠው ይነግሯችኋል:: ስልክ ደውለውለት የሚያውቁት ደግሞ ሁኔታው ሁሉ በደንብ ይገለፅላቸዋል:: ቃሊቲ ወርዳ የቀረችበት ሚስቱን በፅናት፣ በፍቅር፣ በቃሉ… ፀንቶ እየጠበቃት  ያለው ስለሺ ሀጎስ ሙዚቃው ከወጣበት ጊዜ አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ ወደ ስልኩ የደወለ ሁሉ ከወዲያኛው ጫፍ ይህንኑ የሚካኤል በላይነህ ሙዚቃ ያዳምጣል::
በጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ እና በጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ መካከል ያለውን ፍቅር እና ዛሬ ላይ ያሉበትን ሁኔታ የተረዳ ሰው ደግሞ በሙዚቃው ግጥም ውስጥ ያሉት ቃላት ላይ ይበልጥ ይመስጣል:: ለዚህም ነው ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ በአንድ ወቅት ‹‹ትመጪ እንደው›› ሲል እራሱን የቻለ ሙሉ ፅሁፍ ያስነበበን:: ባይሆንማ ኖሮ እዚሁ ጉዳየ ላይ ብቻ በርካታ ተጨማሪ ነገሮች ባነሳሁ ነበር:: ስለሺ የዛሬው ርዕስ ጉዳዬ ብቸኛው ተጠቃሽ አይደለም፤ ከሌሎችም ጋር አብሮ የሚነሳ እንጂ:: ለማንኛውም ርዕዮት እንደምትመጣለት እኛም ተስፋ እናድርግና ወደዛሬው ጉዳዮችን እንዝለቅ::

የእናት እዳ ለልጅ
የኢህአዴግን እዳ የምዘረዝርበትን የዛሬውን ፅሁፌን እንድሞነጫጭር መነሻ የሆነኝ ሌለኛው የሚካኤል በላይነህ ሙዚቃ እንደሆነ ስጠቅስ ሚኪ እራሱ ዘፈኑ ተተርጉሞበት በአሸባሪነት እንዳይከሰስ ትሰጉ ይሆናል:: ኢህአዴግ ምን ገዶት፣ ከፈለገ ‹‹እንዲህ ያለውን ምርጥ አልበምማ ያለ አሽባሪዎች አንዳች ድጋፍ ልትሰራው አትችልም::›› ሊለውና የክስ መዝገብ ሊከፍትበት ይችላል::…መጠርጠር አይከፋም::…ስለዚህ ሁልሽም በጠርጣሪው ፓርቲ ልትጠረጠሪ እንደምትችዪ ብትጠረጥሪ ከጥርጣሬ ቀውስ ቀድሞውኑ ሊታደግሽ ይችላል::

ቅዳሜ ሰኔ 23 ቀን 2005 ዓ.ም ‹‹አሸባሪ›› ወዳጆቼን ለመጠየቅ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቅራቢያ ተገኝቼ የመጠየቂያ ሰዓቱን /6:00 ሰዓት/ መድረስ እጠባበቃለሁኝ:: ሌሎች የፈትያ እና የርዕዮት ጠያቂዎችን ጨምሮ የእማዋይሽ፣ የሒሩት፣ የተፈራ፣ የሀቢባ እና የጫልቱ ጠያቂዎችም ልዩ ተጠያቂዎች የሚጠየቁበትን ስድስት ሰዓት በመጠባበቀ ላይ ናቸው:: ከመካከላችን አንዱ ስልኩን አወጣና ወደሆነ ቦታ ደወለ:: ስልኩን ጆሮወ ላይ አድርጎም፡-
      የሰማይ መሬቱ የባህር ስፋቱ
      እንዳለም ዳርቻ እንደ ‘ርቀቱ
      አይኖችሽን ባይኔ ተዳክሜ እያየሁ
      ስወድሽ ስወድሽ ውዴ ወድሻለሁ፤….
እያለ የገብረክርስቶስ ደስታን ግጥም በዜማ እያዋዛ መዝፈን ያዘ::.. ወዲያውም የስልኩ ጥሪ የሆነውን የሚካኤል በላይነህን ሙዚቃ እያንጎራጎረ መሆኑን ተረዳሁ::… የደወለው ናርዶስ ጋር ነው:: ዘወትር እናቷን እማዋይሽን ለመጠየቅ ከቃሊቲ የማትጠፋው ናርዶስ ዛሬ በአቅራቢያው ስላልታየችው ነበር ይህ ሰው ስልክ የደወለው:: ናርዶስ ግን ቀድማን መጥታ ኖሮ ግቢ ውስጥ በጊዜ ገብታ ሰዓቷን እየተጠባበቀች ነው:: ስለሺ የፍቅሩን መምጣት በተስፋ ሲጠብቅ ‹‹ትመጪ እንደው…›› ሲል፣ ናርዶስ ደግሞ ‹‹ስወድሽ›› በሚል ለእናቷ ያላትን ጥልቅ ፍቅር እየገለፀች ነው::…

ኢህአዴግ ባለ እዳ ከሆነባቸው ዜጎች ውስጥ አንዷ ናርዶስ ናት:: እንኳን መከራን ፍቅርን እንኳን በአግባቡ መሸከም የማይችለው የናርዶስ ጨቅላ እድሜዋ ያለ ጊዜው መከራ እንዲያጎብጠው ሆኗል:: በወጉ እንኳን ያልጠናችው ናርዶስ በ15 አመቷ ኢህአዴግ ከእናቷ ጉያ ነጥሏት ብቻዋን ቀረች:: እናቷ እማዋይሽ ወደ እስር ቤት በአሸባሪነት ተፈርጃ ስትወረወር ናርዶስ ባዶ ቤት ታቅፋ ቁጭ አለች:: ከማትችለው የእናቷ ፍቅር ተነጥላ ባዶ ቤት መልመድ አልሆንልሽ ያላት ናርዶስ ባዶው ቤት የመኖር ዋስትናዋን እንኳን ማረጋገጥ ተሳናት:: በልማት ስም አካባቢያቸወ ፈርሶ ለሁሉም ተለዋጭ ቦታ እና ቤት ሲሰጣቸው ናርዶስ ግን ሰሚ አጣች:: ከእናት አልባነት ወደ ቤት አልባነት ተሸጋገረች:: መከራ ጓዙን ጠቅልሎ የሰፈረባት ትንሿ ናርዶስ ክፉኛ ተረታች:: በአክስቷ ጎትጓችነትና አለሁሽ ባይነት ለትምህርት ወደጅጅጋ አቅንታ አክስቷን ተጠጋች::
ናርዶስ ከጥቂት ግዚያት ቆይታ ቦሀላ የእናቷ ፍቅር ጠራትና ስትበር መጣች:: ትምህርቷን ወደ አዲስ አበባ ለማዛወር ብትሞክርም እሺ የሚላት አጣች:: ዛሬ ናርዶስ አምሳያ ለሌለው የእናቷ ፍቅር ሁሉን ነገር መስዋት አድርጋ ቃሊት ትመላለሳለች:: እኩዮቿ አምረው፣ደምቀውና አጊጠው በሚዝናኑበት ወቅት፣ እሷ እዚህ ሁሉ ነገሯን ለእናቷ ሰጥታ ስለ እናቷ ትኖራለች:: ለእናቷ ሰትል የማትከፍለው አንዳች መስዋትነት የለም::…
አሁን ናርዶስና እናቷ ከሽቦው አጥር ወዲያና ወዲህ ሆነው ሰላምታ እየተለዋወጡ ነው:: እናት በሽቦው ውስጥ ሶስት ጣቶቿን አሾልካ ወደ ልጇ ላከች:: ልጅም ተንጠራርታ የናቷን ጣቶች መሳም:: በተመሳሳይ እናትም በሽቦው ውስጥ ሾልከው ያገኘቻቸውን የልጇን ጣቶች ሳመቻቸው::
ሚካኤልም ማጀቡን ቀጠለ፡-
እንደ ጽጌሬዳ
እንደ አደይ አበባ
እንደ ከርቤ ብርጉድ
እንደ ሎሚ ሽታ
አበባ እንዳየ ንብ
እኔ እወድሻለው
ፍቅርሽን በፍቅሬ
በፍቅርሽ ልቅመሰው፤…



 … ልጅ በፍጥነት እናቷን ከእግር ጥፍሯ እስከ ራስ ፀጉሯ ቃኘቻትና ‹‹ለምንድነው ፀጉርሽን ያልተሰራሽው?›› ስትል በፍቅር ተቆጣች:: እናትም ‹‹ተሰርቻለው እኮ…›› አለች::… ‹‹ያመጣሁልሽን ቀለምስ ለምንድነው ያልተቀባሽው?…›› ናርዶስ እናቷን እንደማኩረፍ ቃጣት:: እናቷ እንደምትፈልገው አልተዋበችላትም፡፡… ይሄኔ አይኔን ወደ ሁለቱም ፀጉር ላይ አሳረፍኩት:: የእናት ፀጉር በወጉ የተያዘና ለኔ እይታ ብዙም ያልከበደኝ ሲሆን፣ የልጅት /ናርዶስ/ ፀጉረ ግን ተንጨባሯል:: ከጊዜ ወደ ጊዜ ሁሉ ነገሯን ለእናቷ በማድረግ እራሷን እያፈዘዘችው መጥታለች::…

ጡት እንዳየ ህጻን
ወተት እንዳማረው፤
ጠጋ በይ ዘመዴ
አፍሽ ህይወቴ ነው፤
አፈር መሬት ትቢያ እንደሚበላው
ገላዬ ገላሽን ሲነካ የሚያልቀው፤…

ይህቺ 20 ዓመት እንኳን በወጉ ያልሞላት ታዳጊ ምን በወጣት ነው ይህንን ሁሉ እዳ /ፍዳ ብለው ይሻላል/ የምትከፍለው? ኢህአዴግስ ቢሆን የዚህችን ልጅ እዳ እንዴት ቢያደርግ ነው ከፍሎ የሚጨርሰው? ቢገደል፣ ቢታሰር፣ ቢሰቀል፣…? እንዴት ይህ የናርዶስን እዳ ይመልሳል? በስርዓቱ ተጠያቂ ሆኖ እዳ ከፋዩስ ማን ነው? እውነት እንዲህ ያለው በደል በፍ/ቤት አልያም በባህላዊ የሽምግልና ስርዓት እንኳን ሊካስ፣ ተመጣጣኝ ፍትህ ሊያገኝ ይችላል? እንጃ እኔ ግን አይመስለኝም፡፡

በፅሁፌ መግቢያ ላይ ያነሳሁት ተስፈኛው ስለሺ (ዛሬ እንኳን ጭራሽ እንዳያገኛት ተደርጓል) ሌላኛው ፍዳ ቀማሽ ሆኖ ከናርዶስ አጠገብ ቆሞ ከፍቅሩ ርዕዮት ጋር በስስት እየተያዩ ያወራሉ:: ከተመደበላቸው ሰዓት ጋርም እሽቅድድም የያዙ ይመስል፣ አንድ ሰኮንድ እንኳን ለአይናቸው እርግብግቢት በመፍቀድ ማባከን የፈለጉ አይመስሉም:: ‹‹የፍቅር አምላክ ይሄኔ ምን ይሰማው ይሆን?›› ስል አሰብኩኝ፡፡… ያፈቀሩትን ሰው በሽቦ ፍርግርግ ውስጥ አድርጎ እንቁልልጭ ማለት ምህረት ያሰጥ እንደሆን እርግጠኛ አይደለሁም::… ስለሺ ስለ ፍቅሩ ብዙ ተሰቃይቷል::… ቤተሰቦቿ ተንከራተዋል::… እና ኢህአዴግ ለስለሺ ምን ቢያደርግ ነው ፍቅሩን፣ ልቡን፣ ግዜውን፣ ውበቱን፣ ሰውነቱን፣ ጉልበቱን፣ ስራውን… መልሶ ሊከፍለው የሚችለው? ምንስ የሞራል ብቃትና አቅም ይኖረዋል? ስለዚህ ኢህአዴግ በምንም መንገድ ከፍሎ የማይጨርሰው ፍዳ /እዳ/ ባለቤት ነው:: ስለሺ ግን አሁንም ዕናቱን፣ ተስፋውን እና ናፍቆቱን በልኩ በተስፋው ዜማ በኩል ሲገልፅ ይሰማኛል:-
      … በናፍቆትሽ እሳት ነድጄ ሳልከሰም
      ባይንሽ በጠረንሽ መልሼ እንዳገግም፤
      ሳዜም እኖራለሁ ፀሎት ስደጋግም
      ካለሁበት ድረስ እግርሽ እንዲረዝም፤
      ልምጣ ያልሽ እንደሆን ቀና ነው ጎዳና
      ልቤ ተመላልሶ ደልድሎታልና፤
      ምኞት የማይደክመው ልቤ ልበ ብርቱ
      ትዝታም አይደለ ተስፋ ነው ቅኝቱ፡፡ …
ትላንትን ብቻ በትዝታ እያላመጠ ለመኖር ሳይሆን፣ ነገንም በተስፋ ይጠብቃታል:: ፍቅሯን ጨምሮ ቤተሰቦቿ ያዩት ፍዳ ስለመከፈሉ እንጃ እንጂ፣ ተስፋቸውስ በከንቱ የሚቀር አይደለም::…

ከፕሬዝዳንታዊው ወግ ጀርባ


በመሐመደድ ሐሰን

ጋሽ ግርማን ለቀቅ! ኢህአዴግን እና ኤፈርትን ጠበቅ!
በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጽ/ቤት የመጎብኘት አጋጣሚው የተፈጠረልኝ በጋዜጠኝነት ሙያ ውስጥ ከተሰማራሁ ቦሃላ ሲሆን፣ እስከ አሁን ባለው ግዜ ውስጥም ለሶስት ግዚያት ያህል ገባ ወጣ ማለት ችያለው፤ ከሶስቱ ቀናት ሁለቱ ወደ አንድነት፣ አንደኛው ደግሞ ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ አምስተኛው በር ፊት ለፊት አከባቢ ወደሚገኘው መድረክ ጽ/ቤት ጎራ ያልኩባቸው ናቸው፡፡ በመድረክ ጽ/ቤት የተገኘነው በ2002 ዓ.ም መጀመሪያ (ከመሐመድ አሊ ጋር) ከአቶ ገብሩ አስራት ጋር ቆይታ ለማድረግ ነበር፤ ሆኖም ግን፣ ከዛሬው ጉዳዬ ጋር ግንኙነት ያላቸው በአንድነት ጽ/ቤት ያደረግኳቸው ሁለቱ ቆይታዎች በመሆናቸው ወደዛው ልለፍ፡፡  
በ 2002 ዓ.ም መጀመሪያ ባምቢስ አከባቢ ወደነበረው የአንድነት ጽ/ቤት ባመራሁበት ወቅት፣ የመጀመሪ የመስክ ስምሪቴ እንደመሆኑ፣ ባገኘሁት ሰው እና ባየሁት ነገር መገረሜ አልቀረም፤ በወቅቱ ቀደምት የፓርቲው አመራሮች መረጃ ለመስጠ በሚያመነቱበት ወቅት አንድ ሰው ያደረገልኝ ትብብር በጣም አስገራሚ የሚባል ነበር፤ ከትብብራቸው ባለፈ የሰውዬው ማንነት በራሱ ይበልጥ ግርምት ፈጥሮብኛል፤ የምፈልገውን መረጃ ከሰጡኝ ቦሃላ ተጨማሪ የሚረዱኝን ጽሁፎች ለመስጠት ያለሁበት ድረስ በመሮጥ መጥተው አቀብለውኛል፤ ኮፒ አልቆባቸው ቢሯቸው በር ላይ የተለጠፈ ወረቀት ገንጥለው ሰጥተውኛል፤…
ትንሽ ቆየት ባልኩ ቁጥር የማስተውለው ነገር ይበልጥ ግርምቴን እያናረው ነው፤ የምሳ ሰዓት ደርሶ ነበርና እኚሁ ሰው አነስ ያለች ሰሀናቸውን ከፍተው እዛው በቢሯቸው ለመመገብ ሲሰናዱ አስተዋልኩኝ፤ የእውነት ነው የምላችሁ ልቤ ‹‹…ጉድ ነው! ጉድ! ጉድ!...›› በሚለው የጂጂ ሙዚቃ ታጅቦ ይደልቅ ጀመር፡፡ እኚህ ሰው የኢትዮጵያ ህገ-መንግስት ላይ ፊርማቸውን ያኖሩት እና ከ6 ዓመት በላይ የቆዩበትን የፕሬዝዳንትነት ስልጣናቸውን በገዛ ፍቃዳቸው የለቀቁት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ናቸው፡፡

በቅርቡ አንድነት ፓርቲ በጸረ-ሽብር ህጉ ላይ እያካሄደ በነበረው ዘመቻ አዘጋጅቷቸው ከነበሩት መርሀ ግብሮች ውስጥ አንዱ ህጉን የሚቃወሙ ሰዎች ፊርማቸውን እንዲያኖሩ ማድረግ ነበር፤ እኔ እና አንድ ወዳጄም በዚሁ ሀሳብ መነሻነት ለመፈረም ቀበና ወደሚገኘው አዲሱ የፓርቲው ጽ/ቤት ጎራ ብለን ነበር፤ በዚህ ግዜም እንደመጀመሪው ሁሉ አንድ ነገር መታዘቤ አልቀረም፤ ወዳጄ ‹‹መቶ አለቃ?›› ሲል ሰላምታ ያቀረበላቸው አንድ ሸምገል ያሉ ሰው ቢሯቸው ውስጥ ቁጭ ብለው፣ አነስ ባለች ሰሀን ዳቦ በወጥ እየበሉ ነበር፡፡ እናም ወዲያው ተሰናባቹ ፕሬዝዳንት አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ (እሳቸውም መቶ አለቃ መሰሉኝ?) በዛው ተመሳሳይ ሰዓት ላይ ሊኖራቸው የሚችለውን የምሳ ሰዓት  እያስታወስኩ፣ ‹‹ሁለቱ መቶ አለቃዎች በምሳ ሰዓት›› ስል አሰብኩኝ፡፡
እርግጥ ነው በቤተመንግስት ውስጥ የሚኖረው የምሳ ሰዓት ቀደም ብዬ ካነሳኋቸው ሁኔታዎች በእጅጉ የተለየና ለንጽጽርም የማይቀርብ ነው፤ ምናልባትም ለአልበርት አንስታይን የአንጻራዊነት ንድፈ ሀሳብ (Reletivity Theory) ጥሩ ማሳያም ጭምር ሊሆን የሚችል ነው፡፡ በምሳ ሰዓት ቤተ-መንግስቱ በጭልፋና ማንኪያ ጩኽት፣ በምግብ አብሳዮቹ ሽር ጉድና መስተንግዶ፣ በምግብ ዓይነቶቹ ብዛትና ጥራት፣ ወዘተ እንደሚደምቅ መገመት አያዳግትም፡፡
ሁለቱም ለዚህች ሀገር ይበጃል ያሉትን በየፊናቸው የሚሰሩ ናቸው፤ ነገር ግን ልዩነታቸው ለመግለጽ እንኳን በማይመች መልኩ የሰፋ ነው፤ መንግስት በተቃዉሞ ጎራ ያሉትንም ያቀማጥል የሚል ጥያቄ ማቅረቡ የማይታለም ቢሆንም፣ ቢያንስ ግን ከስር ከስር በመከተል ስቃያቸውን እንዳያበዛባቸው መመኘት ይቻላል፡፡ ይህንን እና መሰል የዜግነት መብታቸውን ብቻ ቢያከብርላቸው እና ክብራቸውን ቢጠብቅላቸው፣ በቤተመንግስት ውስጥ በወከባ ከሚቀርብላቸው ጮማ በተሻለ፣ በጠባቧ ቢሮ ያለው ነጻነት እና ሽሮ ለእነሱ በእጅጉ የላቀ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡
በተለይ የዶክተር ነጋሶ ጉዳይ ይበልጥ ይረብሻል፤ እሳቸው ሁሉንም ነገር ያደረጉት እና ጠባቧን ቢሮ ከጠባቧ ህይወት ጋር የመረጡት፣ ከምንም በላይ እንደ ሰው በነጻነት መኖር ፈልገው እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል፤ ሆኖም ግን እንደ አንድ ዜጋ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት የነበሩ አንድ ትልቅ ሰው፣ በአንዲት ጠባብ ቢሮ ውስጥ ከመመገባቸው በተጨማሪ፣ ታክሲ ተጋፍተው ሲሳፈሩ፣ የሚኖሩበትን የኪራይ ቤቶች ለቀው እንዲወጡ ሲገደዱ፣ ጥቅማጥቅማቸውን ሲነፈጉ፣ በአንድ ተራ ፖሊስ ሲጎነተሉና ሲታሰሩ፣ በህመማቸው ጊዜ የጤና ዋስትና ሲያጡ፣… ከማየት በላይ ምን የሚረብሽ ነገር አለ?... ይህንን ጉዳይ ይበልጥ እንቆቅልሽ የሚያደርግብን ደግሞ ከሰሞኑ ለተሰናባቹ ፕሬዝዳንት በወር  የ400.000 ብር ቤት መንግስት እንደተከራየላቸው ስንሰማ ነው፡፡
ከተሰናባቹ ፕሬዝዳንት የቤት ኪራይ ጋር በተያያዘ የተነሱት ነጥቦች (እኔ ያየኋቸው)፣ በፕሬዝዳንቱ ስብዕና ላይ ያተኮሩ እና በብሩ መብዛት ግርምት የተፈጠረባቸው ናቸው፤ እኔ ግን ከቤቱ ኪራዩ ጋርም ሆነ ከፕሬዝዳንትነት ዙፋኑ ጋር በተያያዘ መነሳት ያለባቸው ነጥቦች እንዳሉ አስባለሁ፡፡
የቀደሙት ፕሬዝዳንት የስራ ዘመናቸው ወደመገባደዱ በተቃረበበት ወቅት ቀጣይ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ለመሆን እንደሚፈልጉ ይናገሩ የነበሩ እና ለፕሬዝዳንትነት በየመገናኛ ብዙሀኑ ይታጩ የነበሩ ሰዎችን ልብ ብለን ካስተዋልን፣ ቦታው ምን ያህል እንደተናቀ ይገባናል፤ አንዳንዶቹ መደበኛ ትምህርታቸውን እንኳን በአግባቡ የጨረሱ አልነበሩም፤ ህልመኞቹ ሀገር በእግር ፍጥነት አልያም ደግሞ በድምጽ ውበት የሚመራ ያህል ሳይሰማቸውም አልቀረም፤ ብዙዎች በድፍረት ቦታውን ከመመኘት አልተቆጠቡም፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ያላቸውን ዓለም አቀፋዊ ክብር ከግምት ያስገቡት አይመስሉም፤ የገዢው ፓርቲ አሻንጉሊት መሆን ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ሊወተውቱ ሁሉ ቃጥቷቸዋል፡፡… የሆነው ሆኖ ቦታው ምን ያህል እርባና ቢስ እንደሆነ ከደፋሮቹ ድፍረት የተሻለ ሌላ ማሳያ ፍለጋ መኳተን የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡… አዲስ የተሾሙትን ዶ/ርም ይህንኑ በደንብ የሚያጠናክሩልን ይመስለኛል፡፡    
ጋሽ ግርማን ለቀቅ! ኢህአዴግን እና ኤፈርትን ጠበቅ!
እኔ እንደማምነው ጋሽ ግርማ ቀደም ብሎም ቢሆን በቦታው ላይ አልነበሩም፤… ዶክተር ሙላቱም ቢሆኑ ያው ነው፤… ቦታው በኢህአዴግ ስርዓት እና አሰራር ሽባ ተደርጓል፤ ነገር ግን ግለሰቦቹ በቦታው ላይ እስካሉ ድረስ የፓርቲው ፍላጎት በስማቸው ይፈጸማል፤ አሁን ደግሞ ከወረዱም ቦሃላ ለፓርቲው ተጨማሪ ጥቅም ማግበስበሻነት እንዲውሉ እየተደረገ ነው፤ ከሰሞኑ ስንነጋገርበት የነበረው የፕሬዝዳንቱ የቤት ኪራይ ጉዳይ የዚህ አንዱ ማሳያ ነው፡፡
በአሁን ጊዜ በየከተሞች ውስጥ ከምናያቸው ግዙፍ ህንጻዎች በስተጀርባ የባለስልጣናቱ (በተለይ የህወሐት) ስውር እና ግልጽ እጆች አሉ፤ ገንዘቡ ደግሞ ግልጽ ነው ከየትም የመጣ ሳይሆን በተለያየ መንገድ ከሀገሪቱ ሀብት እና ከህዝቡ የተበዘበዘ ነው፡፡… እነዚህ ህንጻዎች በብዝበዛ  ተሰርተው ካለቁ ቦሃላም ለተጨማሪ የሀገሪቱን ሀብት መበዝበዣነት ይዘጋጃሉ፤ በየከተሞቹ ከሚቆሙ ህንጻዎች ጀርባ ያሉት ባለስልጣናቱ፣ ያላቸውን ሀላፊነት ተጠቅመው ህንጻዎቹ ለአንድ መንግስታዊ ተቋም ቢሮነት አልያም ከሰሞኑ ለጋሽ ግርማ እንደተደረገው ለባለስልጣናቱ መኖሪያነት በውድ ዋጋ እንዲከራይ ያደርጋሉ፡፡
በአሁን ሰዓት ብዙ መንግስታዊ ቢሮዎች በዓመት ለኪራይ የሚያወጡት ብር የራሳቸውን ህንጻ መገንባት የሚያስችላቸው ቢሆንም፣ የህወሐት /ኤፈርት/ ስውር እጆች ግን ይህ እንዲሆን የሚፈቅዱ አይደሉም፤ በህንጻ ኪራይ ስም ከመንግስት ካዝና የሚሰበሰበው ጥቅም ዳጎስ ያለ በመሆኑ አሰራሩን ይበልጥ መሰረት ይሰጡታል፤ አንድ መንግስታዊ ቢሮ በወር እስከ ሁለት ሚሊየን ብር ለህንጻ ኪራይ የሚከፍልበት ሁኔታ እየተለመደ መጥቷል፤… ከሰሞኑ እንደሰማነው ደግሞ ጋሽ ግርማ በወር እስከ 400.000 ብር የሚያወጣ ቤት ተሰናድቶላቸዋል፡፡… ይህ የተደረገው ለሰውየው አልያም ለዙፋኑ ካላቸው ክብር የተነሳ አይደለም፤ ይልቅ ከህንጻዎቹ ጀርባ የአንድ ታጋይ፣ባለስልጣን፣የፓርቲው ተቋም፣ ወዘተርፈ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ስላለበት እንጂ፡፡ በቃ እውነታው ይሄ ነው!
የዛሬዋ ኢትዮጵያ መሪዎች እንዲህ ናቸው- ሁሉን ነገር በኢኮኖሚ ሚዛን ላይ ከመስፈር ጋር ፍቅር የያዛቸው፤…ሁሉንም ነገር ከፓርቲ ጥቅም አንጻር ብቻ መመዘን!... ሀገርን ባገኙት አጋጣሚ እና ቀዳዳ ሁሉ መበዝበዝ! … መሬቱን በህገወጥ መንገድ ማገኘት እና ህንጻውን በበዘበዙት ገንዘብ ማሰራቱ አልበቃ ቢላቸው በኪራይ ሰበብም ከስጋዋ አልፈው አጥንቷ ድረስ ይግጧታል!... በቃ እነሱ ይሄው ናቸው፤ ከጠሉና ለፓርቲያቸው ካልበጀህ የቀደመ ፕሬዝዳንት ብትሆንም ግድ የላቸውም፤ ዜግነትህ ሳይቀር ይገፉሀል፤… አገልጋይ/ሎሌ/ ከሆንክ ደግሞ ዳጎስ ያለ ቁሳዊ ጥቅም ይዘጋጅልሀል፤ ባንተ ሰበብም ለፓርቲው እና ሰዎቿ ሲባል ሀገራዊ ብዝበዛው ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡…  
ይሄኔ ነው ታዲያ ጮክ ብሎ እንዲህ ማለት፡-     
እናት ኢትዮጵያ ሞኝ ነሽ ተላላ፣
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ!
የመብላት እና የመበላት ሂደቱ መልክና አይነቱን እየቀየረ ይቀጥላል፤ ግን እስከመቼ?!....    

ኢህአዴጋዊ ጠብሽ


በመሐመድ ሐሰን         (ላይፍ መጽሄት ላይ የወጣ)

አንድ ጎረምሳ ሲጠብሸው ፍሪዙን (አናቱን) ያካል፤ ከዛም ቤተሰቡን አልያም ወዳጆቹን ቀፍሎ ይሔዳል፡፡ ችግሩ መንግስት ሲጠብሸው ነው፤ መንግስት ሲጠብሸው ምኑን የሚያክ ይመስልሀል? ሀገርን፣ ዜጎቿን፣ እና ሀብቷን ካልክ አልተሳሳትክም፡፡ ግን ታዲያ ለመንግስት ከአንድ ጎረምሳ እኩል ‹‹ያካል›› አይባልም፤ ይቧጥጣል እንጂ፡፡ በአሁን ሰዓት የመንግስትን ስልጣን በመያዝ፣ በመንግስት እና በፓርቲ መካከል ያለውን ድልድይ ያፈራረሰው ኢህአዴግ፣ በከፍተኛ ጠብሽ ውስጥ ለመውደቁ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ እውነታውን ለመረዳት አከባቢያችንን ማስተዋል ነው፡፡ ፓርቲው የመታው ጠብሽ ኢኮኖሚያዊ ብቻ አይደለም፤ ይልቅ ፓርቲው የተመታው በሀሳብ፣ በምክንያት፣ በህግ፣ በፍትህ፣ በፖለቲካ፣ በፖለቲከኛ፣ በጋዜጠኛ፣….ጠብሽም ጭምር እንጂ፡፡ እናም ሀገር ምድሪቱን እየቧጠጣት ነው፡፡
ኢኮኖሚያዊ ጠብሽ
አንድ ከመንግስታዊ ተቋም ክስ ተመሰርቶበት የነበረ ወዳጅ አለኝ፡፡ በወቅቱ ተቋሙ እንደከሰሰው ቀረበና በጉዳዩ ላይ ከሀላፊዎቹ ጋር ብዙ ከተነጋገረ ቦሃላ፣ እሱን በማሰልጠን ‹‹አጣን›› ያሉትን ወደ ሀያ ሺህ ብር እንዲከፍላቸው ተስማሙ፡፡ እሱም በውላቸው መሰረት ከወር ደሞዙ ያስቆርጥ ጀመር፡፡ ከበርካታ ወራት ቦሃላ ባለፈው ደወለልኝና ‹‹ባክህ እነዛ ሰዎች እኮ በድጋሚ ከሰሱኝ!›› አለኝ፡፡ ‹‹ደሞ ምን እንሁን ነው የሚሉት?›› አልኩት፤ ‹‹ በድጋሚ አሁን ሌላ ሀላፊ ሲመጣ የቀድሞ ውላችን ተሸሮ ሀምሳ ሺህ ብር እንድከፍል በፍርድ ቤት አስወስነው ውሳኔው ተላከልኝ፡፡›› በማለት ድርጀቱን አማሮ እርግማን የተቀላቀለበት ብሶቱን አካፈለኝ፡፡
በነገራችን ላይ ይህ ጓደኛዬ እንዲህ ያለውን ሁኔታ ከነገረኝ ቦሃላ ፣ በብዥታ ቀደም ብሎ እሰማቸው የነበሩና አሁንም ከየሰው የምሰማቸው አንዳንድ መሰል ጉዳዮች፣ ኢህአዴግ ኢኮኖሚያዊ ጠብሽ ውስጥ መሆኑን እንድገምት አድርጎኛል፡፡ ግምቱ ግን ግምት ብቻ ሆኖ አልቀረም፤ በቅርቡ ስሜቴን የሚጋሩ በርካታ ተጠቂዎች ገጥመውኛል፡፡ መንግስት ገንዘብ ፍለጋ የሰነዶችን አዋራ በማራገፍ ገንዘብ እያሰሰ ነው፡፡ የኢኮኖሚያዊ ጠብሹ ማሳያ ይህ ብቻ አይደለም፡፡
በተለይ ከወቅታዊው የሙስሊሞች ጥያቄ ጋር በተያያዘ ኢህአዴግ በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ እየወሰደ ያለው የእስር እርምጃ የጠብሹን መጠን ለማሳየት እንደ ጥሩ ምሳሌ ሊነሳ ይችላል፡፡ ምዕመናኑን ሰበብ እየፈለገ በየእስር ቤቱ ካጎራቸው ቦሃላ የዋስ መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ያደርጋል፡፡ ታዲያ ዋሱ በገንዘብ ነው፡፡ ከ አንድ ሺህ ብር እስከ ሀያ አምስት ሺህ ብር ለዋስ በሚል እንዲያስይዙ ይጠየቃሉ፡፡ ታዲያ አንዳቸውም ብሩን ካስያዙና ከተፈቱ ቦሃላ ፍርድ ቤት አይቀርቡም፣ ብሩም አይመለስም፡፡ ጸጉርህን እና ኪስህን እያከክ በከንቱ መመላለስ ብቻ ነው መፍትሄው፡፡
ሌላኛው በንግድ ማህበረሰቡ ላይ የተያዘው ተገቢ ያልሆነ ግብር የማግበስበስ ዘመቻ ዋነኛው የኢኮኖሚ ጠብሹ ማሳያና መፍትሄውም ተደርጎ የተወሰደው ነው፡፡ ነጋዴው በሱቁ ካለው (በድርጅቱ) ካለው የእቃ ዋጋ በላይ የሚጠየቅበትን ገራሚ አሰራር እያየን ነው፡፡ ይህ የገንዘብ ጥማቸውን የሀራራ መጠንም ጭምር የሚያሳብቅ ስግብግብነት ሆኖ ተወስዶባቸዋል፡፡ ከደሞዝተኛው ላይ የማይቆረጥ የግብር አይነት የለም፡፡ ሰራተኛው እና መንግስት እኩል ሲካፈሉም እያየን ነው፡፡  
አረ ጉዱ ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ በመለስ ሙት ዓመት (ወር) ስም፣ በመለስ ፋውንዴሽን ምክንያት፣ በአርፋጅ ተማሪ ሰበብ፣ በመንገድ ስራና ጥገና ተሳቦ፣… አዋጡ! አዋጡ! ነው፤ እንደውም እኮ ግዴታም ጭምር ተቀላቅሎበት ነው፡፡ ህዝብ እና ሀገር በፓርቲው ይቧጠጣሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ደግሞ፣ እንዲህ ባለው ሁኔታ የተገኘው ገንዘብ (በተለይ ከግብር) እየዋለ ያለው ፣ፓርቲው ለፖለቲካ መጠቀሚያነት በሚፈልጋቸው እንደ ኮንዶሚኒየም ባሉ የቤት ፕሮጀክቶች ላይ መሆኑ ነው፡፡ ከብዙሀኑ ሰብስቦ ለጥቂቶች የማዋል አይነት አሰራር፡፡ ዓባይም የኢህአዴግን ኢኮኖሚያዊ ጠብሽ በማናሩ በኩል በከፍተኛ ሁኔታ ይጠረጠራል፡፡
ሲጀመር በራሱ የኢህአዴጋዊነት መገለጫ ከሆኑት ነገሮች ውስጥ አንዱ እና ዋነኛው ጠብሽ ይመስለኛል፡፡ እስኪ ኢህአዴግ አሉኝ ከሚላቸው ምናምን ሚሊየን አባላቶች ውስጥ አንተ እንኳን የምታውቃቸውን አስብ፤ ከፈለግክ ቀበሌ ወይም ክፍለ ከተማ ሂድ! አብዛኞቹ (ሁሉም በለው ከፈለክ) አባል የመሆናቸው መነሻ ኢኮኖሚያዊ ጠብሽ ሲሆን፣ በሀሳብ በኩልም ቢሆን እልም ያሉ ጠብሻናሞች ናቸው፡፡

የሀሳብ ጠብሽ
ቀደም ብዬ እንዳነሳሁት በኢህአዴግ ጉያ ስር የተሰባሰቡ ሰዎች በመጀመሪያ ደረጃ ኢኮኖሚያዊ ጠብሻቸውን ለማስታመም ስለሚመጡ፣ የተወሰነ ግዜ ያላቸውን ቀለሃ ይተኩሱና ከዛ ቦሃላ ወደ ትክክለኛው መነሻቸው ይመለሳሉ፡፡ እንደግፍህ ያሉትን ፓርቲ ይደገፉታል፡፡ እንዲህ ያሉት ሰዎች እጣ ፈንታቸው ሁለት ሊሆን ይችላል፡፡ አንድም ምንም ያልገባቸውን ሀሳብ ዝም ብለው ይዘባርቃሉ፡፡ ሚናገሩት ነገር ምንም ደርዝ ላይኖረው ይችላል፡፡ ብቻ ዝም ብሎ ማውራት! እንደ እንትና ማለት ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እንደገደል ማሚቱ ከላይ አለቃ ያለውን ብቻ ማስተጋባት ሁለተኛው እጣ ፈንታቸው ይሆናል፡፡ ማን ነበር ስሙ? አዎ! እንደሱ ማለት ነው፡፡
እንዲህ ያለውን ኢህአዴጋዊ የሀሳብ ጠብሽ ለማስተዋል ብዙም ርቆ መሄድ አያስፈልግህም፡፡ ለምሳሌ ቴሌቪዥን ክፈት፡፡ ጋዜጠኛው ፖለቲከኞቹን ተክቶ የባጥ የቆጡን ሲፖተልክ ትሰማዋለህ፡፡ የሀሳብ ጠብሽ በነገሰበት ማን ስህተቱን ነግሮ ‹‹ሀይ!›› ይለዋል? ዝም ብሎ መሸክሸክ ነው እንጂ! ከሆነ ቢሮ ተጋብዞ የመጣ እንግዳ ካለም ከቻለ የተሰጠውን ያነባል፤ ካልሆነም ባልገባው እና በማያውቀው ሀሳብ ላይ አለማወቅ የቸረውን ድፍረት ተጠቅሞ ይዘባርቃል፡፡
አሁን ደግሞ የመሪ ጠብሹም ክፉኛ ስለጎዳቸው፣ ጠባቂ እንደሌለው መንጋ ፓርቲውን ወደ አደጋ ውስጥ እየከተቱት ይገኛሉ፡፡ የጣሉትን እና የተበለጡበትን አጀንዳ መልሰው አፈሩን አራግፈው ያነሱታል፤ በድጋሚም ግን ይሸነፉበታል፡፡ አሁን ለምሳሌ ሰሞኑን የተከበረውን የባንዲራ ቀን እንደ ምሳሌ ብናነሳ፣ አባባላችንን በደንብ ያስደግፍልናል፡፡ የማይደፈረውን ደፍረው ‹‹ባንዲራ ጨርቅ ነው›› አሉ፡፡ ከዛ ደግሞ ባለፈው ግዜ ከሙስሊሞቹ ጠንካራ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ክፉኛ የሀሳብ ጠብሽ ሲመታቸው፣ ‹‹ባንዲራውን አክራሪዎች አቃጠሉት…›› በሚል ከኔ በላይ ስለባንዲራ ተቆርቋሪ ላሳር አለና ፍረጃውን አጠንክሮ ቀጠለበት፡፡ ግን ብዙ መጓዝ አልቻለም፡፡ በኢዱ ተቃውሞ ላይ ላይ ‹‹ባንዲራችንንማ እንዴት እንደምንወደው እናሳያቹሃለን!›› በሚል ከልጅ እስከ አዋቂው ድረስ በገፍ ይዞ ወጣ፡፡ ድጋሚ እንዳያንሰራራ ሆኖ ተበለጠ፡፡ ይሄኔ ሌላ ስህተት ሰሩ ባንዲራ መቀማት ጀመሩ፡፡… የዘንድሮውን አከባበር ደግሞ እንዳያችሁት ምንም በማይገናኝ መልኩ ባንዲራንና አክራሪነትን አያይዘው በጠብሻናሞቻቸው አማካይነት ሲያደነቁሩን ዋሉ፡፡
የጅል (የሞኝ) ዘፈን ሁሉም አንድ ነው እንዲሉ፣ ዓመቱን ሙሉ ‹‹አክራሪነት፣ሽብርተኝነት፣ መለስ፣…›› በሚሉ ድግግሞሾች ሲያላዝኑብን ውለው ከረሙ፤ በቅርቡም ሚተውት አይመስሉም፤ ይሄን ትተው ምን ሌይዙ ይችላሉ ለነገሩ? ጠብሽ ይሉሀል ሄ ነው! የተገዢ መሳለቂያ እስከመሆን የሚያደርስ ባዶነት!
መብራት ሲጠፋ፣ ጋዜጠኛ ሲታሰር፣ ኔትወርክ ሲቋረጥ፣ ዶላር ስናጣ፣ ውሃ ሲሄድ፣ ስደት ሲበረክት፣ ኑሮ ሲወደድ፣ ሙስና ሰበረክት፣ ሰልፍ ሲከለከል፣ ወዘተ ወዘተ ሁሌ የልብ የማያደርስ ጠብሻናም ምላሽ መስጠት እስከመቼ? ጠብሽ በበረታ ቁጥር ሀገሪቱን እና ህዝቧን እየቧጠጡስ የት ይደረሳል? ኽረ ሼም ነው! መንግስታዊ ጠብሽማ ይደብራል! ሀገርንም ጭምር  ያጠብሻልና ይሰውረን፡፡                   
                            

Friday, October 18, 2013

ማንኩሴዎች ሲበረክቱልን! ከበእውቀቱ ወደ ሀብታሙ



በመሐመድ ሐሰን

‹‹ፍቅር እስከ መቃብር›› በተሰኘው ተዓምራዊ ልብወለድ መጽሀፍ ነው ክቡር ዶክተር ሀዲስ ዓለማየሁ በዛብህ ቦጋለ የተባለ ማንኩሴ ገፀ- ባህሪ ያስዋወቁን፤ የሀዲስ ዓለማየሁ በዛብህ የተሰኘው ስም ለአንድ ኢትዮጲያዊ አዲስ ባይሆንም፣ የበዛብህ የትውልድ አካባቢ ተደርጋ የተሳለችው ማንኩሳ ግን ለብዙዎቻችን አዲስ ነበረች፤ ከዚህ ግዜ ጀምሮ እንግዲህ እኔን ጨምሮ በርካቶች በምናብ ከምንናፍቃቸው አከባቢዎች አንዷ ለመሆን በቅታለች ማንኩሳ፡፡
ከዘመናት  ቆይታ በኃላ ደግሞ  በዕቀቱ ስዩም የተባለ ፀሀፊ ወደ ድርሰቱ ዓለም ገባና፣ ‹‹ክንፋም ህልሞች›› በተሰኘ ስራው ላይ ማንኩሳን ‹‹ ቀበሮ ጀምሮ የተወው ጉድÕድ ትመስላለች›› ሲል ገለፃት፡፡ ያም ሆኖ ግን በምናብ ከምንነጉድባቸውና በአካልም ለመሔድ ከምንuምጥባቸው ቦታዎች አንዷ ከመሆን አላገዳትም፡፡ ምናልባት ብዙዎቻችሁ ወደ ማንኩሳ እንድትነጉዱ የሚያደርጋቸሁ፣ ከበዛብህ ቦጋለ ቀጥሎ በዕውቀቱ ስዩም ይሆናል፤ እሱም በአንድ ወቅት መዓዛ ብሩ የጨዋታ እንግዳ አድርጋ ባቀረበችው ወቅት፣‹‹ከበዛብህ ቦጋለ ቀጥሎ በቅኔ  መንፈስ የሚታወቅ ማንኩሴ  ቢኖር እኔ ነኝ፤›› በሚል ፌዝ አከል ንግግር ማድረጉን አውቃለሁ፤ በእርግጥም ይህንን ንግግር እኔ ከፌዝ ባለፈ እውነታነትን እንዳዘለ ከሚያምኑት ውስጥ አንዱ ነኝ፡፡ ነገር ግን፣ በተለይ በአሁን ሰዓት ማንኩሳ ስትነሳ ከበዛብህ ቀጥሎ ቶሎ ወደ ህሊናዬ የሚመጣው በዕውቀቱ አይደለም፤ ‹‹እና ታዲያ ማንን ልትጠራ ፈለግክ? አንተ ደፋር!›› ካላችሁኝ፣ ምላሼ ስዩም የሚል ነው፤ መምህር ስዩም መሰለ!
ዛሬ በጡረታ ተገልለው ማንኩሳ ላይ የከተሙትና በማርቆስ የእንጊሊዘኛ መምህር የነበሩት የአቶ ስዩም መሰለን ቤተሰብ ስንከተል የምናገኛቸው ወጎች፣ታሪኮች፣ ልማዶች፣ህይወቶች ፣ሰዎች ፣…. ተነግረው የማያልቁ አስደማሚዎች ናቸው፡፡ ‹‹ኤርትራዊ ናችሁ›› ተብለው የተባረሩትና የሰፈሩን ልጆች በጣፋጭ አንባሻቸው ያሳደጉት የአቶ አስፋው ሚስት እማማ ሀለፎም፣ በሱዳን ገዳማት ለረዥም ዘመናት የቆዩትና በወጋቸው መሐል ‹‹የአላህ!.....›› እያሉ ወሬያቸውን የሚቀጥሉት መነኩሴዋ አያታቸው ፣በአካባቢው የነበሩ ጠንካራ ወጎችና ልማዶች፣ በቤታቸው ውስጥ በእሳት ዙሪያ የሚካሔደው የተረትና የግጥም ውድድር እንዲሁም ጨዋታ፣ የአባትና ልጆች ግንኙነት፣ የባልና ሚስት ግንኙነት፣ … ብቻ ቁጥር ስፍር የሌላቸው ብዙ ጣፋጭ ወጎች የሚወጡት ስብስብ ነው በዙሪያቸው ያለው ማህበረሰብ፡፡
ማንኩሴዎችና ማርቆሴዎች ከጥበብ ጋር ያላቸው የመንፈስ ቅርርቦሽ ጥብቅ ሊባል የሚችል ነው፤ ከማንኩሳ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘውና የስዩም ቤተሰብ ሌላኛዋ መኖሪያ በሆነችው ማርቆስና አከባቢዋ ያሉ ሰዎች፣ የጥበብ ፍቅራቸውን ለመግለፅ በሰፈሩ ጉብላሊቶች (የስጡም ልጆችን ጨምሮ) የተደረሱ ድራማዎችና ቲያትሮችን ለማየት ወንበር ከየቤታቸው ተሸክመው ነበር የሚታደሙት፡፡ ታዲያ የማይረባ ስራ ለመለየት ግዜና የጋዜጣ ገፅ አይጠብቁም፤ እዛው መድረክ ላይ ያልጣማቸውን ስራ ያጥረገርጉታል፡፡ ጀማሪዎቹም እንዲህ ያለውን ትችት በመልመዳቸው፣ የተሻለ ነገር ለማምጣት ዘወትር በሚያደርጉት ጥረት ወደ ብስለት ይሸጋገራሉ፤ ሒሳቸውንም እጅ በመንሳት ጭምር ሰጥ ለጥ ብለው ይውÚታል፡፡
ይህ ባህል በአካባቢዋ ሁሉ ተዛምቶ ሳይሆን አይቀርም፣ በባህር ዳርና በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ባህል ማዕከሎች ይቀርቡ ለነበሩ የማይረቡ ስራዎች፣ የአካባቢው ተወላጆች ወደ አቅራቢዎቹ ጫማቸውን ጭምር በመወርወር ነበር ምላሽ የሚሰጡት፡፡ በተለይ ዛሬ በኢትዮጲያ  ቴሌቪዥን ላይ ከኔ በላይ ለኢህዴግ ተቆርuሪ ፣ ለመሪዬ ተቆርuሪ፣ …ላሳር እያለች በሬሳዎች አካባቢ ጭምር በመንጎማለል የምትሳለቀው አንዲት ‹‹ጋዜጠኛ?›› ተብዬ፣ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ የግጥም ስራዎን ታቀርብ በነበረበት ወቅት ምላl ጫማና ጩኸት እንደነበር ፣አንድ ወዳጄ አጫውቶኛል፡፡ በእርግጥ ኢቴቪን ካነሳን አይቀር በዚህ ጣቢያ ውስጥ ከዛ ጥበበኛ ህዝብ መሀል (ማርቆስና አከባቢዋ) ወጥተው ለሆዳቸው ያደሩ ብዙ ሆድ አደሮች እንዳሉ ማስታወሱ ተገቢ ነው፡፡
ቀደም ብዬ በጠቀስኩት መንገድ ጠንከር ያለ የጥበብና የንባብ ባህል ተጠናክሮ ከሚካሔድባቸው ቤቶች አንዱ ነው የመምህር ስዩም ቤት፡፡ እስከ ጥግ ድረስ ነፃነት በሚሰጡ አባትና ወግ አጥባቂ በሆኑት እናት ወ/ሮ ሀገሬ ከበደ መካከል ያደጉት ልጆቻቸው  በእሳት ዙሪያ በሚጋሩት ጥበባዊ ስራ የተለያዩ የአድናቆትና የተግሳፅ አስተያየት እየሰሙ ነው ያደጉት፡፡ በዚህ ቤት ውስጥ ለጥበብ ስራ ማጣፈጫነት ገጸ በሀሪ ፍለጋ ብዙም ርቀው አይማስኑም፤ አካባቢያቸውንና የቤተሰቡን አካል ጭምር ለዚህ የማዋል ትልቅ አስተውሎት አላቸው፤በተለይ አሁን የጎረመሰውና ያኔ በልጅነቱ ኮልታፋ የነበረው ዱኒ አሁንም ድረስ የቤተሰቡ ወግ ማጣፋጫ ነው፡፡ይህ ቤተሰብ የማያባራ የሳቅ ምንጭ ነው፤ ፖለቲከኛው፣ ዘፋኙ፣ ጋዜጠኛው፣…ሁሉም በዚህ ቤት ውስጥ ያለገደብ ወደጨዋታው መድረክ ይዶላሉ፡፡ ከንባብ ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ያለው የመምህር ስዩም ቤተሰብ ውስጥ ሁሉም አንድ አይነት ተሰጥኦ አላቸው የሚባሉ አይደሉም፤ ለምሳሌ ዱኒ በአባቱ የግጥም ችሎታ ይስቃል፤ ይዝናናል፡፡
በንባብ በኩል ሁሉም የየራሳቸው ጣዕም ያላቸው ናቸው፡፡ እናት ወ/ሮ ሀገሬ ከበደ የስለላ መፅሁፍትን አጥብቀው የሚወዱ ሲሆን፣ ከስለላ ጋር በተያያዘ ያላነበቡት ስራ እንደሌለ ከቅርብ ሰው ሰምቻለው፤ በዚህ መነሻነትም አንደኛው ልጃቸው ‹‹ እናታችን የስለላ ስራዎችን አብዝታ ከማንበቧ የተነሳ ልጆን በከፍተኛ ንቃት ውስጥ እየሰለለች ያሳደገች ሰላይ እናት ነው ያለችን፤›› ሲል እውነትን ከፌዝ ጋር ቀልቀል አድርጎ ያስፈግጋል፡፡ ይኸው ልጃቸው በአንድ ወቅት የስለላ ስራዎችን በብዛት በማሳተም የሚታወቁት አንጋፋው ደራሲ ማሞ ውድነህ ሞተው በነበረበት ወቅት፣ የሆነ ሰው መፅሀፋቸውን እንዲዘረዝርለት አጥበቆ ሲጨቀጭቀው፣ ‹‹ ለምን ሀገሬ ከበደ ጋር አትደውልም!›› የሚል ምላሽ ይሰጠዋል፡፡
የመምህር ስዩምን የንባብ ባህል ደግሞ ጤና በራቀው uu ከገለጽነው እብድ ያሉ የመፅሀፍ ቀበኛ ናቸው፤ በዓለማችን ላይ የገዘፈ ስም ያላቸውን የራሽያ ደራሲዎች ስራ አንድ በአንድ እንዳነበቡ ልጆቻቸው ጭምር የሚመሰክሩላቸው መምህር ስዩም፣ በተለይ በመምህርነት ዘመናቸው ትጉህ አንባቢ የነበሩ ሲሆን በወቅቱ የወጡና አሉ የተባሉ ማንኛውንም መፅሀፍት ለማግኘት የማይከፍሉት መዋትነት አልነበረም፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአንድ ወቅት የተፈጠረውን ሁኔታ በፍፁም እንደማይረሳው ልጃቸው በአንድ ወቅት አጫውቶኛል፡፡ መምህር ስዩም በወቅቱ ይከፈልቸው የነበረው ደሞዝ ብዙም የሚያወላዳ አልነበረም፤ ቀልባቸው ግን አንድ መፅሀፍ ላይ አርፏል፤ የመፅሀፉ ጥማት የበረታባቸው መምህር ስዩም ደሞዝ የተቀበሉ እለት፣ ወደ መፅሀፍት መሸጫው ቦታ ያመሩና የደሞዛቸውን ግማሽ ይሰዋሉ፤ አስቡት የመፅሀፉ ብር ተቀንሶ የቀረው ገንዘብ  ከ6 በላይ የነበረውን ቤተሰብ ለአንድ ወር የማስተዳደር  ግዴታ አለበት፡፡
መምህር ስዩም በዚህ መንገድ የሚገዟቸውን ፣የሚዋሷቸውን፣ከቤተመጽሀፍት የሚያገኙዋቸውን ውድ መፅሀፍቶች ልጆቻቸው እንዲያነቡ ያደርጋሉ፤በእርግም አንብበዋል፤ለልጆቻቸውን ከመፅሀፍ ጋር የማቆራኘት ጉጉታቸው ከልጆቹ እድሜም የቀደመም ነበር፡፡ ለዚህ ማሳያ ከሚሆነው እውነታ አንዱ፣ የስድስተኛ ክፍል ተማሪ የነበረው ልጃቸው ሀብታሙን ወደ ላይብረሪ (ቤተ-መፅሀፍት) ይዘውት ይሔዱና ከመደርደሪያው ላይ አንድ መፅሀፍ መርጠው ካነሱ በኃላ ‹‹ይኸውልህ ሀብቴ ! ዘ ኦልድ ማን ኤንድ ዘ ሲ! እንዴት ያለ ድንቅ መፅሀፍ መሰለህ!›› ብለው ወኔ በተሞላበት ንግግር መፅሀፉን ይሰጡታል፤ልጅም መፅሀፉን እነደተቀበለ ‹‹እነዴ ! አባዬ እንግሊዘኛ እኮ ነው!›› የሚል ምላሽ ሲሰነዝር፤እሳቸውም  ጠንከር ባለ ድምጸት ‹‹ሀብቴ ! ምን ነካህ ?ፈረንጆቹ ባንተ እድሜ ይፅፋሉ፣ አንተ እንዴት ላንብበው ትላለህ!…›› ብለው ቁጭት ይጭሩበታል፤እሱም ከዛን ግዜ ጀምሮ እየተንገዳገደ የቻለውን ያህል መግለጥ ይጀምራል፡፡ በዚህ መንገድ የተገነባ ጠንካራ የንባብ ባህል ነው መምህር ስዩም ለልጆቻቸው ያወረሱት፡፡ልጆቻቸውን የምናውቅ ብዙዎቻችን ባላቸው የንባብ ጉጉትና አቅም እንገረም ይሆናል፤መሰረቱ ግን ከልጆቹ በላይ ያነበቡት አባት ናቸው፡፡
ከላይ ስለገለፅነው ጠንካራው የጥበብ ፣የሳቅ(የቀልድ)፣ የንባብ፣ የእውቀት፣…ምንጭ ስለሆነው የስዩም ቤተሰብ ካለምኩኝና ካሰላሰልኩኝ እንዲሁም እውቀታቸውን ከተጋራው በኃላ ነው፣ ከዚህ ጠንካራ ቤተሰብ የተገኘውን ማንኩሴ (በዕውቀቱ ስዩም )የማስታውሰው፡፡ በዕውቀቱ እንዲህ ካለው ከፍታ ላይ ከመውጣቱ በፊት ከቤተሰቦቹ ብሎም ከማንኩሳ ባለፈ ማርቆስ ድረስ ባሉ ጥበብ ወዳጆች ተፈትኖና ተሸልሞ ነው ብቃቱን ያሳየው፡፡ የአንባቢው እና የመንፈስ ጠንካራው ስዩም ልጅ በመሆኑ ነው ዛሬ በዕውቀቱ ሀገሪቱ ላይ ካሉ ፀሀፊዎች ሁሉ ውዱና የምንሳሳለት ፀሀፊ ለመሆን የበቃው፤ ለዚህም ነው በዕውቀቱ ከኢትዮጵያ አልፎ አሜሪካና አውሮፓ ጭምር ያሉ ጥበብ አፍቃሪዎች እንዲናፍቁት ያደረገው፤ ለዚህ ነው እኔም ማንኩሴዎችን አብዝቼ የምናፍቃቸውና እንዲበዙልን የምመኘው፤ለዚህምነው ዛሬ የማንኩሳ፣ ያውም የስዩም ፍሬዎች ሲበረክቱልን በደስታ እየቦረቅኩ ብዕሬን ያነሳሁት፤አዎ ማነኩሴዎቹ የስዩም ፍሬዎች በርክተውልናል፤ የበዕውቀቱ ስዩም የሁለት ግዜ ታናሽ የሆነው ሀብታሙ ስዩም ‹‹17 መድሬና ሀያ ምናምን ቁምጣ ›› በሚለው መፅሀፉ አንባቢው ጋር ደርሷል፤ መፅሀፉን ላነበበና ሀብታሙን በግል ለሚያውቀው፣ ከበዕውቀቱ ስዩምና ከአባቱ ጋር ከፍተኛ የመንፈስ ቁርኝት አላቸው፡፡ ሁለቱም የጠንካራ አባታቸው የመንፈስ ውርሶች ናቸው፤ እንዴት የሚለውን በስፋት የመተንተን ጉዳይ ለሌላ ሰፊ ገፅ የምናመቻቸው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የማውቀውን ያህል ግን በጥቂቱ አወራችኋለው፤ በቅድሚያ ጠንካራው አባታቸውን በቅርቡ በእውቀቱ ስዩም በጉልበታም ብዕሩ እንዴት ስንኝ እንደቋጠረላቸው እንመልከት፡-
           ለአባቴ
ሰው ብቻ አይደለህም፣ካፈር ወጥተህ ላፈር
መላክ ነህ፣ሉሲፈር
ክብርህ ማንነትህ፣ባመጽ የሚታፈር፤
የማትንበረከክ
የማትርመጠመጥ
ከባለጌ ዙፋን
በርጩማ የምትመርጥ
ያለብህር ሰርጎጅ
…ያለሙሴ በትር
በመታገስ ብቻ፣ባህር የምትመትር፡፡
ካዘልከኝ ጀምሮ፣እንኮኮ ጫንቃህ ላይ
ከፍታውን እንጂ፣ ዝቅታውን ሳላይ
እንደንስር መጠቅሁ፣እንደ ምስራቅ በራሁ
የገዛ ክንፎቼን፣እንደ ዳንቴል ሰራሁ፡፡
በርግጥ ደሀ ነበርክ
ከሰላምታ በቀር የማታበረክት
ነጠላህ መናኛ፣ ሰውነትህ የክት፣
በርግጥ ደሀ ነበርክ
የነጣህ የጠራህ
ከጦር ሜዳ ይልቅ ገበያ የሚያስፈራህ፡፡
ቤሳ ባታወርሰኝ አወረስከኝ ትግል
የትም እንዳይጥለኝ ፣ ሕይወት እንደ ፈንግል፡፡
አባየ ብርሃን
ኣባ የምስራቅ በር
ገመና ሸሻጊ፣እንደ ካባ ገበር
አባቴ ባትሆን ይጸጽተኝ ነበር፡፡
በእውቀቱ ስዩም በግጥሙ ላይ የስጋ ብቻ ሳይሆን የመንፈስም ውርሱ የሆነውን የአባቱን ጥንካሬ፣እውነተኝነት፣ትዕግስት፣ጀግንነት፣ውለታ፣ያወረሰውንእውነት፣የአባቱን ብርሀንነት፣…በጥቅሉ የአባቱን ታላቅነት በኩራት ይገልፃል፡፡ ሀብታሙ ስዩምም የአዲሱ መፅሀፍ ማስታወሻነት ደመቅ ጎላ ብሎ  እንዲህ ይነበባል፡-
‹‹ሃገሬ ከበደና መምህር ስዩም መስለ ለሚባሉ የመጀመሪያየም ሆነ የመጨረሻ የኔ ናሙና ለነበሩ ሰዎች፡፡ታውቃላችሁ አልወዳችሁም፤ አመልካቹሀለሁ እንጂ!››
በተመሳሳይ ሁኔታ በመፅሀፉ የምስጋና ገፅ ላይ አንድ ቦታ ላይ’’…. ልጓም የማልወድ ፈረስ ነኝ፤…››ይላል፡፡ ከዚህም ባሻገር በእውቀቱ ግጥም ውስጥ የተገለፀው አባታቸው ማንነት በሁለቱም ላይ ይንፀባረቃል፡፡ የምርም በዕውቀቱ ከአባቱ፣ሀብታሙ ደግሞ ከበዕውቀቱ ያለምንም አካላዊ ጫና የመንፈስ ውርርሳቸው በግልፅ ይታያል፡፡
ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ይህ ፅሁፍ የሁለቱንም ስራ ሆነ የቤተሰቡን ህይወት ሙሉ ለሙሉ አይዳስስም፤ በዕውቀቱን እና ሀብታሙንም በአንድ ሚዛን ላይ እኩል የማሰፈር ተልዕኮ የለውም፡፡ ሀብታሙን በአካል፤ በእውቀቱን ደግሞ በስራው ደንብ አውቃቸዋለሁኝ፤ሁለቱ ከእድሜም ከተጓዙበት የህይወት ጎዳናም አንፃር አሁን ላይ የማይነጻጸሩባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡  አንዱና ዋነኛው፣ በእውቀቱ በሂደት ያካበተው የንባብ ልምድና ሀብት አይደለም ከሁለት ግዜ ታናሹ ከእኩዮቹ ጋርም የሚነፃፀር አይደለም፡፡ በእውቀቱ በእውነትም በንባብ በኩል ከመምጠቅ አልፎ ለተለያዩ የእውቀት ዘርፎች ያለው ተጋላጭነትም የሚያስደምም ነው፡፡
በነገራችን ላይ ይህንን የንባብ ጉዳይ ጨምሮ ከየትኛውም ስራዎቹ ጋር በተያያዘ፣ የበዕውቀቱ ቁጥር አንድ አድናቂ ከሆኑ ሰዎች ውስጥ አንዱ ሀብታሙ ነው፤ በዕውቀቱን በደንብ ስለሚያውቀውም ይመስለኛል፣የሱን ስራዎች በማንበብ በሳቅ እንባ እየዘራ ሆዱን ይዞ ሲንፈራፈር ያየሁት ሰው ሀብታሙ ነው፡፡ ታዲያ በወንድማዊ መንፈስ እንዳይመስላችሁ፣ ሀብታሙ አንድም ቀን የበዕውቀቱ ወንድም መሆኑን አውርቶ አለማወቁ ብቻ ሳይሆን፣ መሆኑም ጭምር በፍፁም እንዲታወቅበት አይፈልግም፡፡ እሱ እራሱን ችሎ በራሱ መንገድ ተገምግሞ አቅሙን ማሳየት የሚፈልግ ትጉህ ነው፡፡ ለዚህም ነው ከአባታቸው በወረሱት ጥንካሬ፣ በዕውቀቱ በራሱ ጥረት እዚህ እንደደረሰ ሁሉ፣ ሀብታሙም ወደ አዲስ አበባ ሲመጣ ከነበረው ሂደት ጀምሮ መጽሀፉ እስከታተመበት ባሉት ሶስት አመታት ድረስ በፍፁም በእውቀቱን ተደግፎት አያውቅም፡፡ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ የተለያዩ ቦታዎች ስራ ሲጀምር፣ በዕውቀቱ እንደማንም ስራውን ካየ ቦሃላ ነው እውነቱን የሚረዳው፤ ለማመን ቢከብድም የሀብታሙ መፅሀፍ ማተሚያ ቤት እስገባበት ድረስ በዕውቀቱ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ ከባህሪያቸው፣ ካለባቸው ውጥረት እንዲሁም ከሌሎች በግልጽ ከማይገቡኝ ምክንያቶች ጋር ተያይዞ ወንድማማቾቹ በአካል የሚገናኙት አልፎ አልፎ ነው፡፡ ያም ሆኖ ታዲያ ነፍሶቻቸው አንድ እስኪመስሉ ድረስ አጥብቀው ከመቆራኘታቸው የተነሳ መንገዳቸውና የሚመሳሰሉባቸው ነገሮች ይበዛሉ፡፡
ሁለቱም አሁን ላለው የየራስቸው ከፍታ ከመድረሳቸው በፊት በተመሳሳይ መንገድ ጥበብን ባገኙት ክፍተት ሁሉ በመስራት እየተሸለሙ ነው የመጡት፡፡ በዕውቀቱ ማርቆስ ውስጥ ፅሁፎች እያሸነፉለት ይሸለም የነበረ ሲሆን፣ በአንድ ወቅት በቦታው በእንግድነት የተገኙት ሰአሊ እሸቱ ጥሩነህ ይመስሉኝል የለበሱትን ጃኬት አውልቀው ሸልመውታል፡፡ ሀብታሙም ጎንደር ዩንቨርስቲ ውስጥ መድረክን ከመምራት አንስቶ በሚያቀርባቸው ጥበባዊ ስራዎቹ ተደጋጋሚ ሽልማቶችን አግኝቷል፡፡
ወደ አዲስ አበባ እንደመጣም አንድ አመት ባልሞላ ግዜ ውስጥ ታላቅየው በዕውቀቱ በተደጋጋሚ ስራዎቹ ወዳሸነፋለት ፖፑሌሽን ሚዲያ ሴንተር በማምራት ተወዳድሮ ስራው ለህትመት በቅቶለታል፣ ሽልማትም አግኝቷል፡፡ በትምህርቱም በኩል ሁለቱም በተመረቁበት  መስክ አልተሰማሩም፤ በእውቀቱ በሳይኮሎጂ፣ ሀብታሙ ደግሞ በህግ ነው የተመረቁት፡፡ ሀብታሙ እንደውም ወደ ስልጠናው  ማእከል ገብቶ ብዙ ከገፋበት በኋላ ነበር ነፃነትን ፍለጋ ጥሎ በመፈርጠጥ አሁንም ድረስ ላልቆሙ ተደጋጋሚ ክሾችና ተጨማሪ እዳዎች ጭምር የተዳረገው፡፡
ሁለቱም በተመሳሳይ መልኩ ጥበብን በተለያየ ቅርፅ ይከውኗታል፤ በእውቀቱን ከልጅነቱ ጀምሮ ለህትመት እስካበቃችው ስራዎች ድረስ ብንከተለው ተዋናይነት ፣ ተውኔት ፀሀፊነት፣ አጭርና ረዥም ልብ-ወለድ ደራሲነት፣ ወግ፣ኮሜዲ፣ ግጥምና ስዕል ውስጥ የምናገኘው ሲሆን፣ ጅማሮውም ጋዜጠኝነትን መሞካከር ነበር፡፡ በእውቀት ለመጀመሪያ  ጊዜ ወደ ለንባቢዎቹ ያደረሰው በ1995 ዓ.ም “ኗሪ አልባ ጎጆዎች”  የተሰኘውን  የግጥም ስብስብ ሲሆን፣ “የበረሀ ጠኔን” የመሰሉ ድንቅ ፍልስፍናን ያዘሉ ግጥሞቹ የተፃፉት ገና  የዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዓመት ተማሪ በነበረበት ወቅት ነው፡፡
ሀብታሙም ወደ አዲስ አበባ የመጣው በመጀመሪያ ደረጃ ጋዜጠኛ ሆኖ ለመቀጠር ሲሆን፣ እስከ አሁንም ድረስ ይህንኑ ስራውን እየሰራ ጎን ለጎንም ቢሆን እንደወንድሙ ሁሉ ውስጡ ያሉትን ቅርጾች እያሳየን ይገኛል፡፡ ከጎደር ዩቨርሲቲ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የተለያዩ የፊልም ጽሁፎችን እየሰራ ያለው ሀብታሙ አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ  ከስራው በተረፈው ግዜ ወደ “ብሉ ናይል” የፊልምና የቴሌቪዥን አካዳሚ ተወዳድሮና በሱ አቅም ከፍተኛ የሚባለውን ክፍያ (በወር 800 ብር) እየፈጸመ የፊልም ጥበብ ትምህርቱን አጠናቆ ተመርቋል፡፡  ሀብታሙ ነፃነቱን ማንም እንዲነካበት የማይፈልግ ሰው በመሆኑ አንዳንዴ ነውጥ ቢጤም ያምረዋል፤ ከፍ ሲል ደግሞ ብስጭቱን በስእል ጭምር  ይገልጻል፡፡  አንድ የማስታውሰውን እውነት እዚህች ጋር ላወጋችሁ ወድጃለው፤ግዜው እኔና ሀብታሙ በአንድ የሬድዮ ጣቢያ ውስጥ በጋራ የምንሰራበት ወቅት ነበር፤ ታዲያ ቤቱ ዘወትር ስብሰባ የሚበዛበትና ነፃነቱንም የሚጋፋው ስለነበር፣ ረዘም ያለው ስብሰባ እየተካሄደ ባለበት ሰዓት ሀብትሽ አቀርቅሮ የሆነ ነገር ይሞነጫጭራል፤ በኋላ ስብሰባው ተጠናቆ የተቀመጠበት ቦታ ላይ ጥሎት የተነሳው ወረቀት ላይ ያየሁት ስዕል የሚገርም ነበር፤ በአንድ የማይክራፎን ሀውልት ላይ ጋዜጠኛው በገመድ ተሰቅሎ የሚያሳይ ስዕል ነበር የሳለው፡፡ ከዚህ በኋላ ተደጋጋሚ የስዕል ሰራዎችን ሲሰራ ማስተዋል ችያለው፡፡ በሌላ በኩል ሀብታሙ አጭርና ረዥም የሬዲዮ ድራማዎችን፣ ጭውውቶችን፣ ወግ፣ የዘፈን ግጥም እና ግጥሞችን የሚፅፍ ሲሆን፣ እንደ በእወቀቱ ሁሉ ቀድሞ ለማሳተም አዘጋጅቶት የነበረው የግጥም ስራውን ነው፤ ነገር ግን ሁል ግዜም “አብዝቼ ማዳመጥ የምፈልገው ስሜቴን ነው” የሚለው ሀብታሙ፣ በቅድሚያ 17ቱን መድፌና ሀያ ምናምኑን ቁምጣ ሊያቀብለን ወዷል፡፡ 
በአሁን ሰዓትም ከሬድዮ ጋዜጠኝነቱ ጎን ለጎን ቀድም ብሎ ወንድሙ ይሰራበት በነበረው የቀድሞው “ሮዝ”  የአሁኑ “አዲስ ጉዳይ” መጽሄት ላይ ፌዝ (ሳቅ) ያዘሉ ቁም ነገራም ወጎቹን እያስኮመኮመን ይገኛል፤ ይህ ቦታም የተገኘው ያለ ወንድሙ እገዛ ሲሆን፣ በእውቀቱ ጽሁፉን ያየው ከአንባቢዎች እኩል መጽሄቱ ገበያ ላይ ከዋለ በኋላ ነበር፡፡ 
ነፃነታቸው ትልቅ ስንቅ የሆናቸው ሁለቱ የስይቲ (በሀብትሽ አገላለፅ) ፍሬዎች፣ በፁሁፋቸው ውስጥ የራሳቸው የሆኑ ጣእሞችና መልኮች ያሏቸው ልባም ፀሀፊዎች ናቸው፡፡ ሳቅ እንደጎርፍ ከሚፈስበት ቤት የተገኙት ማንኩሴዎች (ማርቆሴዎች) በሀገራችን ላይ ሳቅ ያንሳል ብለው ያምናሉ፤  ለዚህም ይመስላል የሁለቱም ጾሁፎች ውስጥ የፌዝ ፍጆታ ከፍ ባለ መጠን ጥቅም ላይ የሚውለው፤ ታዲያ ፌዞቹ ጥርስን ብቻ ሳይሆን አእምሮንም ከፈት (ነቅነቅ) የሚያደርጉ ናቸው፡፡ በተለይ ከፍ ያሉ የፍልስፍናም ሆነ ሌሎች ሀሳቦችን በብቃት በማንሳት ደረጃ በእውቀቱ ዳገቱ ላይ ብቻውን የተቀመጠ ቢሆንም፣ “አማረኛን (ቃላትን) በተለየ ገጽ” በማየቱ በኩል ሁለቱም የተሳካላቸው ፌዘኞች ናቸው፤ በተለይ ደግሞ ሀብታሙ ይህንን ዘመን ይበልጥ ሰለሚቀርበው እንዲህ ያለችውን ፍተላ ተክኖባታል፡፡
እነዚህ የስዩም ፍሬዎች ጥበብን ተጠምተዋታል፣ አጣጥመዋታል፣አድገውባታል፣ ፈትሸዋታል…በመሆኑም አሁን ላይ ለጥበብ ያላቸው ክብርና በራስ መተማመናቸው ብቃታቸውን በደንብ ይገልጸዋል፡፡  በይበልጥ በእውቀቱ ሀገራችን ውስጥ ብዘም በጽሁፍ ብቻ መኖር ባልተለመደበት ሁኔታ እሱ የሙሉ ጊዜ ፀሀፊ ከመሆኑም ባሻገር፣ፈተናውን እንደሚያልፍም ጭምር ቀደም ብሎ በልበ ሙሉነት ይናገር ነበር፡፡ “የተለያዩ ስራዎችን በመሞከር አዲስ ደሴት (ህዋ) ለማሳየት እፈልጋለሁ…አንባቢው ትንሽ ነው ግን እንፈጥረዋለን!”  በሚል እርግጠኝነት ሁኔታውን ሲገልጥ የተደመጠው በእውቀቱ፣የእውነትም ትንቢቱ የሰመረለት ይመስላል፤  በአሁን ሰዓት ማንም የሱንም ሆነ የወንድሙን ስራዎች ይናፍቃል፡፡ ባህልን፣ ፖለቲካን፣ ሀይማትን፣ ታሪክን… ሁሉንም ናጥ አድርገው በእውቀትና በፌዝ ይመረምሩታል፤ እኛንም ወደነሱ ምናብ አስጥመው ያመራምሩናል፡፡
ለማንኛውም የገባሁበት የቤተሰብ ማዕበል በቀላሉ የሚወጣበት ባለመሆኑ፣ እንደምንም ብዬ ባልተገባ አጨራረስ ጥጌን ካልያዝኩ የጋዜጣዋ ሙሉ ገፆች ላይበቁኝ ነው፡፡ እንዲህ ያለው  ተናፋቂ ቤተሰብ ደግሞ በተለይ እንደባለቤቶቹ የተባ ብእር ባላቸው ልጆች ቢገለፅ ይበልጥ ይጣፍጣል፤  እንዲያም እንዲሆን እንጠብቃለን፡፡ እኔ ግን ጉዳዩን እዚህች ጋር ልቋጨውና፣ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ የሀብታሙ ስዩም “17 መድፌና ሀያ ምናምን ቁምጣ”  የተሰኘውን መጽሀፍ በሌላ ቀን እንደምመለስበት ቃል በመግባት ብንሰነባበት እመርጣለሁ፡፡ ታዲያ ክረምትን ጠብቀው በጭን ብቻ ሊያሞቁን የተመኙ ቀሽም ፀሀፊዎችና መጽሀፎች ገበያውን በሞሉበት ሰዓት የደረሰልንን “17 መድፌና ሀያ ምናምን ቁምጣ”ን እንድታነቡት ስጋብዛችሁ በልበ ሙሉነት ነው፤ እኔ ሀብትሽ ገላግሌ ብየዋለሁኝ፤ ዘመናችንን በደንብ አድርጎ ከሽኖታል፡፡ የቻላችሁ የአንድ ቀን የግማሽ ኪሎ ስጋ ዋጋችሁን ለመጽሀፉ ብትሰዉ፣  እንደማትቆጩ አሁንም በእርግጠኝነት ደግሜ አረጋግጥላችኋለሁ::