Tuesday, February 4, 2014

በዳኛቸው ላይ የተሰነዘረ መርህ አልባ "ትችት?"

በመሐመድ ሐሰን




መንደርደሪያ፡-
ረቡዕ ታህሳስ 9 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣው "ሰንደቅ" ጋዜጣ ላይ ዘሪሁን ሙሉጌታ የተባለው የጋዜጣዋ ባልደረባ "መለዮ አልባው፤ምሁር " ሲል በዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ላይ ጽፎ ነበር፡፡ ይህንን ተከትሎም ጸሀፊውን ክፉኛ በማውገዝ የፃፉ በርካቶች ናቸው፡፡ እንደ "ፌስ ቡክ" ያሉ ማህበራዊ ድረ-ገጾች ያለፈው ሳምንት ዋነኛ መነጋገሪያ ከነበሩት ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ይኽው ፅሁፍ ነበር፡፡
የዚህን ጽሁፍ ይዘት ተከትሎ ግመሾቹ አስተያየት ሰጪዎች ዘሪሁንን (ፀሀፊውን) በወያኔነት ሲፈርጁት፣ አንዳንዶቹ ከተስፋዬ ገብረ አብ ጋር አመሳስለውታል፤ አብዛኞቹ ደግሞ ዳኛቸው ለምን ተነካ በሚል ስሜት የተጫነውን ሀሳብ ሰንዝረዋል፤ የተቀሩት ደግሞ ሰማያዊ ፓርቲን ነፃ ለማውጣት ሲሉ ዳኛቸውን በአደባባይ ለመስቀል ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን እኔ ካየኋቸው ፅሁፎች ውስጥ አንዳቸውም ዘሪሁን ባነሳው ሀሳብ ላይ በመንተራስ ያቀረቡት ጠብ የሚል ሀሳብ የለም፡፡…
እኔ እንደማምነው ዘሪሁንን በወያኔነትና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች የፈረጁት ሰዎች ዳኛቸውን በመውደድ ብቻ ከሆነ ስህተት ነው፡፡ ዘሪሁን የመጻፍ መብቱ የተጠበቀ ነው፡፡… እኔ በበኩሌ ዳኛቸው ፍፁም አይነኬ (የማይፃፍበት) ሰው ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ ነገር ግን ሲጀመር ሀሳብ ይዘን መነሳት አለብን፡፡… የዚህ ጽሁፍና ጸሀፊ ዓላማም ዘሪሁንን በመተው ያቀረበውን ሀሳብ መሞገት ነው፡፡
የነገሩ መነሻ፡-
ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ያረፉበትን 100ኛ ዓመት ለመዘከር በሚል እሁድ ታህሳስ 6 ቀን 2006 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ የውይይት መድረክ ያዘጋጃል።በውይይቱ ላይ ሀሳብ እንዲያቀርቡ ከተጋበዙት እንግዶች ውስጥ አንዱ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ነው። እናም ዶክተሩ "የሰንደቅ ጋዜጣ መቅረፀ ድምፅ ይነሳልኝ…” ይላል፡፡ በቃ የዘሪሁን ጽሁፍ መነሾ ይህ ነው፡፡ እኔም በዚህ መነሻነት የተጸፈውን የዘሪሁንን ጽሁፍ ነው መፈተሸ የፈለኩት፡፡
ሚዛናዊነት እና ምክንያታዊነት
ጸሀፊው ዘሪሁን በጽሁፉ ውስጥ ይበልጥ የተቆጨውና የተብሰለሰለው ዳኛቸው ከሚዛናዊነት እና ምክንያታዊነት አፈንጧል ብሎ ስላሰበና የኢትዮጵያ ፕሬስን መፃኢ እድል በዛች ክስተት ማየቱ ነው፡፡… ኢዚህች ጋር ሌላውን ትተን ጸሀፊው እራሱ ባነሳው ሚዛናዊነት እና ምክንያታዊነት የራሱን ጽሁፍ እንገምግመው፡-
ዘሪሁን ጽሁፉን ሲጽፍ ከፊትለፊቱ የስድብ ዝርዝር (ሜኑ) ያስቀመጠ ነው የሚመስለው፡፡ ወገቡን ይዞ ስድቦቹን ያዥጎደጉዳቸዋል፡፡… ሲቅበዘበዙ፣ የሚዲያ ቂመኛ፣ መሸታ ቤት ካልሆነ…፣ እብሪተኞች፣ በቀለኝነት፣  ያዙኝ ልቀቁኝ ማለታቸው፣ ተለዋዋጭ ባህሪ፣ ቃርመው የሚያመጡትን “ኀሳብ”፣ ዘመቻ ማካሄዳቸው፣ ቂም፣ በቀል፣ በትር..፣ ምሁር ተብዬው፣ በቂም በቀለኝነት የታወረ ምሁር፣ ሆደ ሰፊነት የሌላቸው፣ ማመዛዘን የማይችሉ “ፊደላዊ ምሁር”፣ “የአደባባይ ምሁር” ብለው ራስዎትን እንደሾሙ፣ በቲፎዞ ጭብጨባ ስካር ውስጥ ከገባ “ምሁር”፣ የእርስዎን ትንሽነት መድገም፣ እንደሳቸው ትንሽ ላለመሆን፣…"
ጸሀፊው ጨካኝ፣ አረመኔ፣ ጉተታ የበዛበት፣… ሀሳቡን በመያዝ ዳኛቸውን ወደታች ለመጎተት ይዳክራል፡፡ ዳኛቸው ላይ ከየትም ያገኘውን ጭቃ ይወረውራል፡፡ ይሄኔም የተነሳበትን የምክንያታዊነትና የሚዛናዊነት ነጥብ ገደል ይሰደዋል፡፡ የተወሰኑ ማሳያዎችን እንምዘዝ፡-
1.      በጽሁፉ አምስተኛ አንቀጽ ላይ "… ይህን ያደረኩት እንደሳቸው ትንሽ ለመሆን ባለመፈለግ ነበር።…" የሚል ሀሳብ ሰፍሯል፡፡ ዘሪሁን ምክንያታዊነቱን እንዲያረጋግጥልን የተወሰኑ ጥያቄዎችን እንሰንዝር፡- እውን ዶክተር ዳኛቸው ትንሽ ነው? ከሆነስ የአሁኑን ጨምሮ በሌሎችም እትሞቻችሁ ላይ ቀዳሚና ሰፊ ሽፋን የሚሰጠው ለምንድነው? ትንሽ ከሆነ መቅረጸ-ድምጹን ቀድሞውኑ ለምን ማስቀመጥ አስፈለገ? ትንሽ ሰው ፍለጋ መቅረጸ ድምጽ አዝሎ ያለበት ድረስ መሄድ ምን ይሉታል? ጸሀፊውስ ለትንሽ ሰው ይህን ያህል መብሰልሰል ለምን አስፈለገው? ...

2.     ወረድ ብሎ በሰባተኛው አንቀጽ ላይ የሰፈረውን ሀሳብ ደግሞ እንየው፡- " ….. “ያለፉት ሃያ አንድ ዓመታት ፖለቲካ” በሚል ርዕስ ያቀረቡትን ሰፊ ሐተታ በብቸኝነት ዘግባ የነበረችው ሰንደቅ ጋዜጣ ነበረች። በዛን ወቅት ለጋዜጣውም ሆነ ንግግራቸውን በፅሁፍ መልክ አደራጅቼ ያቀረብኩት እኔ በመሆኔ በግል ስልኬ በመደወል ጭምር “እንዲህ ነው ጋዜጠኝነት” ሲሉ አድናቆት አዥጎድጉደውልኝ ነበር።….  ያዙኝ ልቀቁኝ ማለታቸው የሰውየውን ተለዋዋጭ ባህሪ ያጋለጠ ክስተት ነበር።"

እዚች ጋር ትንሽ ሰፋ ያለ ሀሳብ እናነሳለን፤ በቅድሚያ ግን አሁንም ጥያቄ እንሰንዝር፡- ዘሪሁን ይህንን አንቀጽ ያነሳው የዳኛቸውን ተለዋዋጭ ባህሪ ያሳይልኛል በሚል ነው፡፡ "አድናቆት ገለጹልኝ…" ያለው ነገር እውነት ቢሆን እንኳን፣ እሱ የጠቀሰው ነገር እንዴት የዳኛቸውን ተለዋዋጭ ባህሪ ያሳያል? በአንድ ወቅት ዘሪሁንን አደነቀ፣ አሁን ደግሞ ሰንደቅን ተቸ፤ ዘሪሁንና ሰንደቅ ምን አገናኛቸው? በአንድ ወቅት ጥሩ ሲሰራ የተደነቀ ሰው ሲያጠፋም እንዲሞገስ ይሻል?...
ሌላው በሰባተኛው አንቀጽ ውስጥ ከሰፈረው ነጥብ ጋር በተያያዘ ላነሳው የምፈልገው፣  “ያለፉት ሃያ አንድ ዓመታት ፖለቲካ” በሚል ርዕስ ሰንደቅ ላይ የወጣው ጽሁፍ "ጥሩ ነው" የተባለበትን ምክንያት ነው፡፡ በወቅቱ ጽሁፉ ከመውጣቱ ቀደም ብሎ ዳኛቸው ከቀደመ ተሞክሮው በመነሳትና ሀሳቡ እንዳይዛባበት ሲል ሊረዳቸው እንደፈለገ ይነግራቸዋል፡፡ ከተወሰኑ የስልክ ልውውጦች በኋላ ይስማሙና ዘሪሁን ጽሁፉን አመጣው፡፡ ዳኛቸውም ከአሉላ ጥላሁን ጋር በመሆን ጽሁፉን ያስተካክሉትና ባነበብነው መልኩ ጥሩ ሆኖ ሊቀርብ ችሏል፡፡ ይህ ሲሆን እንደ አጋጣሚ ሆኖ እኔም ስምምነት ላይ እስኪደርሱ በቦታው ላይ ነበርኩኝ፡፡        
3.     "…. እኔም ዶ/ሩ ከላይ በተቀመጠው የተጋነነ ገለፃ መጠን በየዋህ ልቦና አደንቃቸው ነበር። ዳሩ ግን ይህ ሁሉ የተባለላቸው ሰው ማመዛዘን የማይችሉ “ፊደላዊ ምሁር” ሆኑብኝ።…" ይህ የጸሀፊው ሀሳብ በተለያዩ አንቀጾች ላይ ተደጋግሞ ተነስቷል፡፡ ለገጽ ቁጠባ ሲባል ሁለት ነገሮችን ብቻ አንስተን እንለፍ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የጸሀፊው አድናቆትና የዳኛቸው ምሁርነት የሚጸናው ዳኛቸው ከዘሪሁን ጋር እስከተስማማ ድረስ ብቻ ነው፡፡ መመዘኛው ከሱ ጋር ያላቸው ግንኙነት መሆኑ ነው እንግዲህ፡፡ ሌላውና ዋነኛው የምንረዳው ጉዳይ ቢኖር ዘሪሁን በሚቃረም ሀሳብ የሚመረቅን መሆኑን ነው፡፡ ይህ ደግሞ ዝቅ የሚያደርገው ጸሀፊውን እንጂ ዳኛቸውን አይደለም፡፡    

4.     የዶክተሩን ምሁርነት ጸሀፊው መካድ ወይም መጠራጠር የሚጀምረው ከርዕሱ ነው፡፡ ምክንያት ግን የለውም፡፡ የዳኛቸውን ትልቅነት ለማሳየት ከሱ አይጠበቅም በሚል እምነት በርካታ ምክንያቶችን ሲዘረዝር፣ አውርዶ ሲጥለው ግን ምንም ማሳያ ሳያቀርብ አላዋቂ ነው ከሚል ድምዳሜ ላይ ይደርሳል፡፡… አንድ ቦታ ላይ የጠቀሰውን ጽሁፍ ለማሳያነት እናንሳው፡-
“ዶ/ር ዳኛቸው ተነቦ የማያልቅ መጽሐፍ ነው። ለብዙ ተዋስኦች ጤናማ ገዢ  ኀሳቦች አሉት። የኢትዮጵያን ታሪክንም አብጠርጥሮ ያውቃል። ፍልስፍና ለእርሱ ክህሎት ነው። ልክ እንደፈረንሳዊ ፈላስፋ በሀገርኛ የሥነ-ጽሁፍ ውጤቶች አጅቦ ታላላቅ የፍልስፍና ቲዎሪዎች ለብዙዎች በሚገባና በሚማርክ መልኩ ያቀርባል”
ይህንን ጽሁፍ ሲሰነቅር ምንም አይነት ማብራሪያ አይሰጠንም፡፡ ይልቅስ በደፈናው በሰፈረው ሀሳብ ላይ በመሳለቅ ለማለፍ ይሞክራል፡፡ እኔ በመግቢያዬ ላይ ጭምር እንደገለጽኩት አንድ ሰው ሀሳብ ይዞ ከተነሳ ማንንም ሊተች ይችላል፡፡ ዝም ብሎ በደፈናው ሳይመረምሩ ግን ማድነቅም ሆነ ማጣጣል ተገቢ አይደለም፡፡
እኔ በግሌ ዳኛቸው ተነቦ የማያልቅ መጽሀፍ ነው፣ በሀሳቦቹ ውስጥም የኢትዮጵያን ችግሮች ማየትና መመርመር ይቻላል፣ ታሪክንም ሆነ ፍልስፍናን ጠንቅቆ ያውቃል፣…ከሚል እምነት ባለፈ በግል ተነሳሽነት ሀሳቦቹን መርምሬ በመጽሀፍ መልክ እያዘጋጀኋቸው እገኛለው፡፡ ሌላው ወገን ደግሞ ከፈለገ ተቃራኒውን ሀሳብ አንስቶ በምክንያት መሞገት ይችላል፡፡ ችግር የሚሆነው በስሜት እና በንዴት ውስጥ ሆኖ ብዕር መጨበጥ ነው፡፡     


5.     ቂምና በቀል የሚለው አገላለጽ በጽሁፉ ውስጥ አብዛኛው ቦታ ላይ ተጠቅሷል፡፡… ዘሪሁን ዳኛቸው እርምጃውን የወሰደው በቂም በቀል ነው ብሎ ያምናል፡፡ ከዚህ የምንረዳው እነ ዘሪሁን ቂም የሚያሲዝ አንዳች ነገር ሰርተዋል እንደማለት ነው፡፡ ከሰሩ ደግሞ አንድም ቦታ አልተጠቀሰም፡፡

በሌላ ቦታ ላይ እንዲሁ "የግል ቂም በቀል ግን የለንም…" ይላል፡፡ አንድ ሰው እንዲህ የሚያደርገው በቂም በቀል ነው ብሎ ካመነ በኋላ ነው የሚገረመው፡፡ ስለዚህ የሚገረመው ስለሌላቸው ነው ማለት ይቻላል፡፡  በጽሁፉ ቀደም ያለው አንቀጽ ላይ ደግሞ "በኛ ላይ ዘመቻ ከፈቱብን…" የሚል ነገር ሰፍሯል፡፡ ዘሪሁንን እዚህች ጋር እንይዘዋለን፡፡ እራሱን ከሰንደቅ ጋር ሰፍቷል፡፡ ሌላውን ችግር ማየት አልፈለገም፡፡ ስለ ሰንደቅ ሌላ ሚዲያ ላይ ማውራት ዘመቻ ሲሆን እነሱ ግን ስለ ዳኛቸው የፈለጉትን ሲሉ መብት ይሆናል፡፡

6.     በሰንደቅ ጋዜጣ ላይ ለዳኛቸው ማስተባበያ ተሰራለት የተባለበት መንገድ በጣም አስገራሚ ሊባል የሚችል ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡- "… በኋላም መስከን ሲጀምሩ አማላጅ በመላክ ጭምር በዘገባው ላይ ሌላ ሰው በምንጭነት ተጠቅሶ “የብአዴን አባል ናቸው” የሚለው አገላለፅ ተገቢ ባለመሆኑ፣ ለጊዜውም ማረጋገጫ ያልተገኘለት በመሆኑና በቀጣይም ከእሳቸው ጋር ሊኖር የሚገባውን ጤናማ ግንኙነት ለመፍጠር ሲባል ማረሚያው ወጥቶላቸዋል።"
እንግዲህ ከዘሪሁን ገለጻ እንደምንረዳው ሰንደቆች ማስተባበያ የሚያወጡት የሙያ ግዴታ ሆኖባቸው ሳይሆን መስከን ለጀመረ፣ አማላጅ ለላከ፣… ነው፡፡ በዚህ አንቀጽ ውስጥ ሌሎች በርካታ ችግሮች ያሉ ሲሆን፣ በገደምዳሜም ቢሆን ዳኛቸውን ከብአዴን ጋር በግድ የማጣበቁ ሂደት አሁንም ተጠናክሮ የቀጠለ ይመስላል፡፡    

ከምክንያታዊነት ባለፈ በዘሪሁን ጽሁፍ ውስጥ የምናገኛቸው የተዛቡ እውነታዎች ብዙ ናቸው፡፡ ዳኛቸው የ"ፌስ ቡክ" ገጽ እንዳለው ተደርጎ የቀረበው መረጃና እራሱን የአደባባይ ምሁር እያለ ይጠራል የሚሉትን ስህተቶች ለአብነት ያህል መጥቀስ ይቻላል፡፡ ዳኛቸው ከኮምፒተር ጋር ብዙም ግንኙነት የሌለው ሲሆን፣ የአደባባይ ተዋስኦና የአደባባይ ምሁር የሚሉትን ሀሳቦች እነ ዘሪሁን በአግባቡ አልተጠቀሙባቸውም፡፡
ዘሪሁን እዚህ ሁሉ ስህተት ውስጥ ከመግባቱ በፊት ግን ዶክተሩን እዛው መድረክ ላይ "ለምን ድምጼን አትቅዳኝ አልክ?" ብሎ ቢጠይቀው ምን ነበረበት? ምናልባት ይህንን አድርጎ ቢሆን ኖሮ በፈለጉ ጊዜ የሰጡትን መለዮ በፈለጉ ጊዜ ከማንሳት ዳግም ስህተት ይታደጋቸው ነበር፡፡ ከመለዮዋ ጋር በተያያዘ አንድ ወዳጄ ያለውን ላስታውስ፡-
"እነኚህ ልጆች መለዮ የሚወዱ ከሆነ መተቸት ያለባቸው መለዮ በአደባባይ የሚያውለበልብን መሪ ነው እንጂ ዳኛቸውማ ባርኔጣውን የሚያውለበልብብበት አደባባይ ከየት አምጥቶ?!"
 ከመብት አኳያ፡
እንደ አሜሪካ ባሉ ያደጉ ሀገራት ውስጥ አንድ ሰው ንግግር በሚያደርግበት ወቅት በግልጽ የሚሰራ ህግ አለ፤ ማንኛውም ተናጋሪ ሲጋበዝ አብሮ concent form (የይሁንታ ቅጽ) ይቀርብለታል፡፡ ድምጹ እንዲቀረጽ፣ ፎቶ እንዲነሳ፣… ፈቃደኛ መሆኑን የሚጠይቁ ዝርዝር መረጃዎች በፎሩሙ ላይ አሉ፡፡ እንደ ግለሰብ የመወሰን መብት የግለሰቡ ነው፡፡
ከዚህ ተነስተን የዳኛቸው እና የሰንደቅ ጉዳይ ላይ ጥያቄዎች መሰንዘር እንችላለን፡፡ አንድ ግለሰብ አንድን ሚዲያ "ድምጼን አትቅረጸኝ" ሲል መብቱ ነው ወይስ የፕሬስ አፈና እየፈጸመ? ድምጹን መቅረጽ ሰውዬ የሚሰጥው ወይስ የሀገሪቱ ህገ-መንግስት የሚሰጠው መብት?... ዘሪሁን መልሱን ካገኘው እስኪነግረን መጠበቅ ነው፡፡
መደምደሚያ
ዘሪሁን በጋዜጣዋ ውስጥ የተለያዩ ጉዳዮችን በመድፈር የተሻለ ጋዜጠኛ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ምናልባት ግን ከኋላው ያሉ ግፊቶች አንዳንዴ ትክክለኛውን መንገድ እንዲስት እያደረጉት ይሆናል፡፡ ስለ ፕሬስ ነጻነት የመቆርቆር ስሜቱን ብጋራም የምር የምንታገል ከሆነ ግን በነጻው ፕሬስ ስም ተቋቁመው ያሉትንም ጭምር ነው መቃወም አለብን፡፡ ስራው መጀመር ያለበት ከቤታችን ነው፡፡ ሰንደቅም እራሷን ትመርምር፡፡ የፕሬስ አፈናውን ከሚያግዙት አንዱ በነጻው ፕሬስ ስም የሚንቀሳቀሱ አስመሳይ ጋዜጦችም ጭምር መሆናቸውን ማመን ይኖርብናል፡፡ ምናልባት በዚህ ጉዳይ ሌላ ጊዜ እመለስበት ይሆናል፡፡ ለማንኛውም ግን የዘሪሁንን መዝጊያ ተውሼ ልሰናበት፡፡ ረጅም ዕድሜ፣ ጥንካሬና ኃላፊነት ለኢትዮጵያ ፕሬስ!

ምሁራኑ ሠልጣኝ፣ ሹመኞች አሰልጣኝ የሆኑበት ዩኒቨርሲቲ ሆኗል

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ




(ዕንቁ መጽሄት)

መጽሔታችን የአገራችን የትምህርት ሁኔታበከፍተኛ ደረጃ ችግር ላይ የወደቀ መሆኑን በመገንዘብ፣ የችግሩን ጥልቀት ለማወቅና የመፍትሄ ሃሳቦችን ለማስቀመጥ በዘርፉ ጥናትና ምርምር ካደረጉ ምሁራን ጋር ተከታታይ ውይይቶችንስታደርግ ቆይታለች፡፡ በዚህ ዕትማችንም ውይይቱን በመቀጠል ከዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጋርስለትምህርት ፍልስፍና፣ ስለዩኒቨርሲቲ ተልዕኮና ስለሌሎቸ ተያያዥ ጉዳዮች ቆይታ አድርገናል፡፡ ዶ/ር ዳኛቸው ለአብዛኛው የመገናኛ ብዙኃን ተከታታይ እንግዳ ስላልሆኑ ማስተዋወቅ ያለብን አይመስለንም፡፡ ውይይቱን እነሆ፡-
ዕንቁ፡-ውይይታችን በዩኒቨርሲቲባህሪና ትርጉም እንጀምር፡፡ ለመሆኑ ዩኒቨርሲቲ ምን ማለት ነው?
ዶ/ር ዳኛቸው፡-ከሁሉ አስቀድሞ ይኼ ጥያቄ ለአንዴና ለመጨረሻ መልስ የሚሰጠው ሳይሆን በተለያየ ጊዜና በተለያየ የባህልና የአመለካከት አውድ ውስጥ ተፈትሾ ለመግለጽ የሚሞከር ጉዳይ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ በባህሪው የሕዝብ (‘ፐብሊክ’) እና የግል (‘ፕራይቬት’) የሆነ ልዩ ተቋም መሆኑን መገንዘብ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡እንደሕዝብ ተቋምነቱ በጥናትና ምርምር ዘርፍ ተሰማርቶ ለማኅበረሰቡ ይውላሉ ወይም አስፈላጊ ናቸው የሚላቸውን ነገሮች በማበርከት አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡ እንደግል ተቋምነቱ ደግሞ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲ የራሱ የሆነ ግብና ዕቅድ አንግቦ ለሰው ልጅ መንፈሳዊና አዕምሯዊ ብልጽግናንናበአጠቃላይ ዕውቀትን ለማጎናጸፍ የተቋቋመማዕከል ነው፡፡
አሁን የበላይነት ወደያዘው የአገራችን የትምህርት ፍልስፍና ስንገባ፣የዩኒቨርሲቲዎች ሕልውና የተመሰረተበትን የግል ጥሪና ፍላጎት ወደ ጎን ገሸሽ በማድረግ ተቋማቱን የሕዝብ አገልግሎት አቅራቢ ብቻ ለማድረግመንግሥትና የዩኒቨርሲቲዎቹ የበላይ አስተዳዳሪዎች ቆርጠው ተነስተዋል፡፡በመሆኑም ለማኅበረሰቡ “ቀጥተኛ ጥቅም” አይሰጡም ያሏቸውን እንደፍልስፍና፣ ታሪክ፣ ሥነ-ጽሁፍ፣ ቋንቋና ሌሎች የሥነ-ሰብዕ ትምህርቶች እንዲቀጭጩ መደረግ ብቻ ሳይሆን ተማሪዎች አልመረጡም በሚል ፈሊጥ የቅድመ-ምረቃ ፕሮግራሙ ወደመዘጋት እየደረሰ ነው፡፡
ዕንቁ፡-የዩኒቨርሲቲን ተፈጥሮና ጠባይ ከሞላ ጎደል ለመመልከት ትንሽ ወደታሪክ መመለስ ይኖርብናል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ለመሆኑዩኒቨርሲቲ እንደ ተቋም እንዴት ተጀመረ?
ዶ/ር ዳኛቸው፡-ይኼ ጥያቄ ማንም ሰው እንደሚረዳው ሰፋ ያለ ትንታኔና ገለጻ የሚያስፈልገው ነው፡፡ ሆኖም ግን ጥቂት ነገሮች ለመግለጽ ያህል፣ በዚህ መስክጥናት ያደረጉትምሁራንእንደሚነግሩን ዩኒቨርሲቲ አውሮፓበ13ኛው እና በ14ኛው ክፍለ ዘመን ከደረሰችበት የመንፈስ፣ የባህል፣ የፍልስፍና…ወዘተ ሥልጣኔ የመነጨ ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ታሪክ ዙሪያ ከጻፉት ምሁራን መካከል እውቅናን ያገኙትና በሰፊው የሚጠቀሱት‘ቻርልስ ሆሜር ሀስኪንስ’ (Charles Homer Haskins) ናቸው፡፡እንደሳቸው አቀራረብ ዩኒቨርሲቲ ከጥንታዊ ግሪኮችና ከሮማውያን ሥልጣኔ ጋር ግንኙነት ቢኖረውም በይዘቱናበጠባዩ የመካከለኛው ዘመን ውጤት ነው፡፡
ከአዕምሯዊ ይዘቱ አካላዊ ወደሆነው ቅርጹናአደረጃጀቱስንመጣ፣ ‘ሀስኪንስ’ በታሪክ ድርሳናቸው ላይእንዳብራሩትለዩኒቨርሲቲ (ግቢ) መፈጠር ምክንያት ከሆኑት ውጫዊ ሁኔታዎች መካከልበወቅቱ ተማሪዎችን የገጠማቸውየቤት ኪራይ ዋጋ መናር አንዱ ምክንያት ነበር፡፡ በዚያን ጊዜብዙ ተማሪዎች ትምህርት ለመቅሰም ወደከተማ ይጎርፉ ነበር፡፡ የተማሪዎች ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ የቤት ኪራይ ዋጋም በጣም እየናረ ሄዶ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ተማሪዎች የሚከፍሉትን የቤት ኪራይ ወጪ ለመቀነስ በአንድ ላይ መሰባሰብና በጋራ በመሆንተደራድረው የቤት ኪራይ ማስቀነስ ጀመሩ፡፡ ይሄ አንዱ ምክንያት ነው፡፡
ሌላው ምክንያት ደግሞ ከአስተማሪዎች የሚመጣው ችግር ነበር፡፡ ይኸውም በአንድ በኩል ገንዘብ እየተቀበሉ ከማስተማር ሥራቸው የሚጠፉ መምህራን ነበሩ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ይኼ ነው የሚባል የትምህርት ዝግጅት ወይም የማስተማር ችሎታ ሳይኖራቸው “መምህራን ነን” የሚሉም ነበሩ፡፡ በዚህ ምክንያት ተማሪዎች ተሰብስበውና ተቋም ፈጥረው አስተማሪዎችንሕጋዊ ግዴታ ያስገቧቸው ጀመር፡፡የትምህርት ዝግጅታቸውን የሚያሳይ ሰርተፊኬት መጠየቅምተጀመረ፡፡ ይህ ሰርትፊኬት ቀስ በቀስ ለዲፕሎማና ለዲግሪ መፈጠር አስኳል ሆነ፡፡
ዕንቁ፡- አንደኛው የዩኒቨርሲቲ ተልዕኮ ዕውቀት ማመንጨት ነው ካልን፣ በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ የዕውቀት ድርሻ ምን ይመስላል?
ዶ/ር ዳኛቸው፡-የዩኒቨርሲቲን ተልዕኮና የእውቀትን ድርሻ በሚመለከት ሁለት አበይት የሆኑ ክርክሮችና አመለካከቶችአሉ፡፡አንደኛው፣ ከ300 ዓመት በፊት በአጠቃላይ ስለትምህርትና ስለዕውቀት ጠቃሚነት የጻፉት (የሳይንስ አብዮት ጀማሪዎች ከሚባሉት አንዱ)እንግሊዛዊው ሮጀር ቤከን እንዳስተማሩትዕውቀት ከተግባር ተለይቶ ሊታይ የማይችል፣ ለሰው ልጅ የኑሮ ደረጃ (በጤና፣በእርሻ …ወዘተ)አስተዋጽኦ ማድረግ ያለበት ነገር ነው፡፡በቤከን እምነት ዕውቀት የዕድገት ወይምየኑሮ ማሻሻያ መሳሪያ ነው፡፡ እንዲያውም ብዙ ጊዜ የሚጠቀስላቸው አባባል እንደሚነግረን ለእርሳቸው‹‹ዕውቀት ማለት ሀይል ነው››፡፡
ወደ ሁለተኛው አመለካከት ስንመጣ ደግሞ ከመቶ ዓመታት በፊት “The idea of the University” በሚል ርዕስ ወሳኝ ድርሳን የጻፉትን ካርዲናል ኒውማንን እናገኛለን፡፡ እንደ እርሳቸው አመለካከት ዕውቀት የራሱ ተልዕኮ አለው፡፡ እንደ መገልገያ መሳሪያ ብቻ ሊታይ አይገባውም፡፡ ዕውቀት የሰውን ልጅ አዕምሮ የሚኮተኩትና ሰውን የተሟላ ፍጡር የሚያደርግ ነው፡፡
እነኝህንሁለትየአመለካከት ዘይቤዎች መሰረት አድርጎ አሁንም አልፎ አልፎ ክርክሩ ቢቀሰቀስም፣ባለንበት ዘመንአንድ ዩኒቨርሲቲ የተሟላ ነው የሚባለው ቢያንስ ቢያንስ የሚከተሉትን ሦስትዕቅዶች አንግቦ ሲንቀሳቀስ ነው፡፡ ይኸውምየመማር ማስተማር ሂደት የሚከናወንበት፣ ዕውነት ላይ ለመድረስ ጥናትና ምርምር የሚደረግበትና በልዩ ልዩ መስክለማኅበረሰቡ አገልግሎት የሚሰጥበትተቋም ነው፡፡በመሆኑም ምርጫው የሮጀር ቤከን“ጥቅማዊ” መንገድ ብቻ ወይም የካርዲናል ኒውማን“አዕምሮን ማበልጸግ”የተናጠል አስተሳሰብ አይደለም፡፡
አሁን በአገራችንመንግሥት እየተከተለ ያለውንየትምህርት ፍልስፍና ስንመለከት፣መንግሥት ዩኒቨርሲቲዎችችግር-ፈቺና ቁሳዊ ጥቅምን ማምጣት የሚችሉመሆን አለባቸው ብሎ ያምናል፡፡ ይኼም ማለት፣ትምህርት ራሱ በራሱ በጎና አስፈላጊ ነገር ሳይሆን መንግሥት ላቀደው የትራንስፎርሜሽን ፕሮጀክት አጋርና አካል መሆን አለበት ብሎ ስለሚያምን ነው፡፡ዩኒቨርሲቲውን በሚመለከት አንድ ትልቅ እንደ ደንቀራ ሆኖ የገጠመን ችግር ይኼ ነው፡፡በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ወደፊት በሚቀጥለውዕትም በሰፊው እንመጣበታለን፡፡ ከወዲሁ ግን ከችግሩ አኳያ አንድ ሁለት ነገሮች ብቻተናግሬ ልለፍ፡፡ በሌላ ጉዳይም ላይ ተደጋግሞ እንደሚታየው ሁልጊዜም በባህላችን መካከለኛ መንገድ ከመምረጥ ይልቅ ነገሮችን ከአንድ ወይም ከሌላ ጥግ ብቻ የማየት ግድፈት አለብን፡፡
ሁለተኛ፣ገዥው ግንባር በሌሎች ጥያቄዎችም ላይ እንደሚያደርገውችግር ብሎ ለሚያነሳቸው ጉዳዮች በሙሉ አንድ ብቸኛ መፍትሄ እንዳለ አድርጎ የማቅረብ አባዜ አለበት፡፡እስከሚገባኝ ድረስ ‹‹ከቀረበው የመፍትሄ ሃሳብ ውጪ የተለየ አቀራረብ ሊኖር አይችልም›› የሚለው ወይም ደግሞ ‹‹አማራጭ የለም››የሚለው አመለካከት ምርጫ የሚያሳጣ ብቻ ሳይሆን የአዕምሮ ነጻነትን በእጅጉየሚጋፋም ነው፡፡ እንዲያውም በሕግ የሰው ልጆችን አስተሳሰብ ከመገደብ የበለጠ ጫና የሚፈጥረውና ነጻነት ገፋፊ የሚሆነው በተወሰነ ጥያቄ ዙሪያ አማራጮችን ዘግቶ ልክ አንድ ብቸኛ መፍትሄ እንዳለ አድርጎ የማቅረብ አካሄድ ነው፡፡ ይኼ ‹‹እኔ ካቀረብኩት የመፍትሄ አማራጭ ውጪ ሌላ መንገድ ሊኖር አይችልም›› የሚለው አካሄድ ዩኒቨርሲቲዎችንአንድ አቅጣጫ ብቻ እንዲከተሉእያደረጋቸው ነው፡፡
ዩኒቨርሲቲ የሰው ልጅ በረዥም ታሪኩ ያከማቻቸውየአዕምሮ ውጤቶች ተጠብቀው የሚቀመጡበት፣ ለአዲሱ ትውልድ የሚተላለፉበትና በታሪክ ውስጥ የተነሱ ጥያቄዎች የሚፈተሹበት፣ የሚመለሱበት…ወዘተ ማዕከል ነው እንጂ የፖለቲካ አስተዳደሩ ወሳኝ ናቸው የሚላቸውን ጉዳዮች ብቻ እንግቦ የሚንቀሳቀስ ተቋም አይደለም፡፡ አንድ ዩኒቨርሲቲ ‹‹ተልዕኮዬ ለማኅበረሰቡ አገልግሎት መስጠት ብቻ ነው›› የሚል ከሆነ ሕልውናውን እንደዩኒቨርሲቲ ያጣል፡፡ዩኒቨርሲቲ ዕውቀት ፈልገው የሚመጡት ተማሪዎች ማኅበረሰቡ ሊያቀርብላቸው ወይም ሊያስተምራቸው የማይችለውን ትምህርትና ተሞክሮ የሚቀስሙበት አምባም ነው፡፡
ዕንቁ፡-በዘመናችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያለው ወይም የበላይነት የያዘው ትምህርት ፍልስፍና ምንድን ነው?
ዶ/ር ዳኛቸው፡-ወደ አሁኑ ዘመን የትምህርት ፍልስፍና በምንገባበት ጊዜ ብዙ ጸሐፍትአራት ዋና ዋና ንድፈ-ሃሳቦችን ያቀርባሉ፡፡የመጀመሪያው መሠረታዊነት ወይም ‘ፐረኒያሊዝም’ የሚባለው አስተሳሰብ ነው፡፡ ይኼን አስተሳሰብ የሚያራምዱ ምሁራን እንደሚሉት የሰው ልጅ ተፈጥሮ (በየትኛውም ቦታ ቢኖር) ተመሳሳይ ነው፤ ዕውቀት የትም ቦታ አንድ አይነት ነው፡፡ስለሆነም የሚሰጠው ትምህርትም አንደ አይነት ወይም ተመሳሳይ መሆን አለበት፡፡የሰው ልጅ ምክንያታዊ እንስሳት ነው፤ ይህ ምክንያታዊነቱ ግን መኮትኮት አለበት፡፡የአስተማሪው ተቀዳሚ ሥራ ደግሞየሰውን ልጅ ምክንያታዊነት መኮትኮት ነው፡፡ትምህርት ዘለዓለማዊ የሆነ ዕውነትን የሚያስተምር ነው፤ ለኑሮ የሚያዘጋጀ መሳሪያምነው፤የሰው ልጅ ወሳኝ ወይም መሠረታዊ የሆኑ እንደሥነ-ጽሁፍ፣ ታሪክ፣ ሒሳብ፣ የተፈጥሮ ሳይንስ፣ ፍልስፍና፣ ሥነ-ጥበብ …ወዘ ትምህርቶችን መማር አለበት፡፡እንዲሁምተማሪዎች ያለፈውን (ሊቃውንትትተውት ያለፉትን) ዕውቀት መማርና መመርመር አለባቸው፡፡
ሁለተኛው፣አመለካከት ደግሞ ‘ፕሮግረሲቪዝም’ የሚባለው ነው፡፡ይኼን አስተሳሰብ የሚያራምዱ ምሁራን እንደሚገልጹት፣ ትምህርት በየጊዜው እየጎለበተ የሚሄድ ነገር በመሆኑ መምህራን ራሳቸውን በዕውቀትና በማስተማር ዘዴ በየጊዜው ማሻሻልአለባቸው፤ትምህርት ራሱ ሕይወት ነው እንጂ ለሕይወት የሚደረግ ዝግጅት አይደለም፤ማወቅ ማለት መተንተንና የሕይወት ተሞክሯችንን መረዳት ማለት ነው፤ ትምህርት ከተማሪው ፍላጎት ጋር መዛመድ አለበት፤ ተማሪው ሌላ ሰው “ይህን ተማር” ስላለው ሳይሆን የሚፈልገውንና ለእርሱ አስፈላጊ የሆነውን ትምህርት ነው መማር ያለበት፤ዕውቀት ተፈላጊ የሚሆነውአንድ ነገር ልናደርግበት ስንችል ብቻ ነው፤የመምህሩ ሚና ማማከር እንጂ አቅጣጫ ማስያዝ አይደለም፤ ትምህርት ቤት ውድድርሳይሆን ትብብርና መደጋገፍየሚፈጠርበት ቦታ ነው፤ ነጻ የሆነ የሃሳብ ልውውጥ ሊፈጠር የሚችለው በዴሞክራሲ ብቻ ነው፡፡
ሦስተኛው፣ አመለካከት ‘ኢሴንሻሊዝም’ የሚባለው ሲሆን፣ አመለካከቱንየሚያራምዱ ምሁራን እንደሚሉት የሰው ልጅ ተምሯልየሚባለውመሠረታዊ የሆኑ ትምህርቶችን ሲያውቅ ነው፡፡ መማር ከፍተኛ ጥንካሬ የሚጠይቅ ነገር ነው፤መማር የማንፈልገውን የትምህርት ዓይነት መማርን ጭምር የሚያካትት ሲሆን ለመማር ደግሞ ‘ዲሲፕሊን’ በጣም አስፈላጊ ነው፤ትምህርት የሚሰጠው “ተማሪው ምን ይፈልጋል?” የሚለውን መሠረት አድርጎ ሳይሆን “ለተማሪው ምን ያስፈልገዋል?” የሚለውን ተከትሎ መሆን አለበት፡፡ ተማሪውየሚማረው የማይፈልገውን ትምህርት እንኳን ቢሆን በሂደት እየተማረ ሲሄድ ይወደዋል ብለው ያምናሉ፡፡የመማር ማስተማሩ ሂደት የሚያርፈውበአስተማሪው ላይ ነው፤ስለዚህ አስተማሪው ወሳኝ ነው፡፡ ትምህርት ሰዎችየውስጥ አቅማቸውን እንዲያወጡ የሚረዳ መሳሪያነው፡፡
አራተኛው፣ አመለካከት‘ሪኮንስትራክሽኒዝም’ይሰኛል፡፡ ትምህርት አዲስ የኅብረተሰብ ሥርዓት (social order) ለመፍጠር ማገልገል አለበት፤ ትምህርት ማኅበረሰቡን ለመለወጥና ለመሻሻልመዋል አለበት፤ ትምህርት የተሻለ የኑሮ ግብ የምንመታበት መሳሪያ ነው፤…ወዘተ የሚሉትን ሃሳቦች የሚያራምድ አመለካከት ነው፡፡
ዕንቁ፡-ከላይየተመለከትናቸውየትምህርትንድፈ-ሃሳቦች ከጥንታዊው እና ከአሁኑ ዘመን የኢትዮጵያ የትምህርትፍልስፍና ጋር እንዴት ይዛመዳሉ?
ዶ/ር ዳኛቸው፡-ከሁሉ አስቀድሞ ይኼ ጥያቄ በጣም ተገቢ ጥያቄ ነው፡፡ለጥያቄውመልስ ለመስጠት ሦስት በዚሁ ጉዳይ ላይ የተጻፉ ድርሳናትንመመልከቱ ተገቢ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ አንደኛ የዛሬ 45 ዓመትገደማ ዶ/ር ኃይለገብርኤል ዳኜ በ“ውይይት” መጽሔት ላይ“የኢትዮጵያ የትምህርት ፍልስፍና” በሚል ርዕስ የጻፉት ጽሑፍ፣ ሁለተኛ፣የዶ/ር ሀይሉ ፉላስ “knowledge and Its Attainment in the Ethiopian context”(The Ethiopian Journal of Education June 1974 vol.7 no.1) የሚለው ጽሑፍና ሦስተኛ፣ዶ/ር ተሾመ ዋጋው የጻፉት“The Development of Higher Education and Social Change an Ethiopian Experience” (1990) የሚለው መጽሐፍበጣም ጠቃሚ ድርሳናት ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡
እነኝህን ሦስቱን ድርሳናት በምናይበት ጊዜ፣ጥንታዊው የኢትዮጵያ የትምህርት ፍልስፍና ከላይ ‘ፐረኒያሊዝም’ ብለን ከጠቀስነው የትምህርት ፍልስፍና ጋር በእጅጉ የተዛመደመሆኑንእንረዳለን፡፡የጥንታዊ ኢትዮጵያ የትምህርት ፍልስፍና በመሠረታዊነትበክርስትና ወይም በእስልምና አስተምህሮት ላይ የተመረኮዘ በመሆኑ ስለእግዚአብሔር ጠባይ፣ የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ጋራ ስላለው ግንኙነት፣ ስለዓለም አፈጣጠር ….ወዘተያለቀለት ወይም ዳግመኛ ምርምር የማይጠይቅና በቅዱሳን መጽሐፍት ላይ ተመርኩዞ የሚጠና ነው፡፡ ዶ/ር ኃይለገብርኤል ከሃይማኖት አበው ጠቅሰው እንደጻፉት ‹‹ነአምን ዘእንበለ ተኅሥሦ››(ሳንመረምር ሚስጥራቸውን እንቀበላለን) የሚለው አባባል ይኼንን ነጥብ በሚገባ ያብራራዋል፡፡ይኼ አንደኛው አስተምህሮት ነው፡፡
ሁለተኛው፣ አስተምህሮት ዓለም በሁለት ነገሮች እንደተከፈለችው ሁሉሰውም በሁለት ነገሮች የተከፈለ ነው የሚለው ነው፡፡ የዓለም አከፋፈል ሰማያዊና ምድራዊ ሲሆን የሰው ልጅ አከፋፈል ደግሞ ነብስና ሥጋ ላይ የተመረኮዘ ነው፡፡ሰማያዊ ዓለሙ ምድራዊ ዓለሙን እንደሚመራ ነብስ ደግሞ ሥጋን እንድትመራ ይጠበቃል፡፡የቀለም ትምህርት ዓላማው ቅዱሳት መጽሐፍትን እያስተማረ ለሚመጣው ዘለዓለማዊ ዓለም ማዘጋጀት ነው፡፡
ሦስተኛ፣ አስተምህሮት ደግሞ ይህች ዓለም አላፊና ጠፊ በመሆኗ ከንቱ ናት፤ ሰማያዊው ዓለም ግን ዘለዓለማዊ ደስታን ይሰጣል የሚለው ነው፡፡ይኼ እንግዲህ ቁሳዊ ብልጽግናንና ዕድገትንአያበረታታም፡፡ዶ/ር ኃይለገብርኤል ይኼን አስተሳሰብ በሚመለከትሲጽፉ ‹‹ባህላችን ቀለም ለተማረ ሰው ከእጅ ሠራተኛና ከገበሬ የበለጠ ደረጃ ሰጥቶታል›› ይላሉ፡፡
በኔ እምነት በአክሱም ዘመነ መንግሥት ትልቅ ቦታ የነበራቸው በቴክኒክ፣ በግንባታ/ምህንድስና፣ በልዩ ልዩየእደ-ጥበብ ሥራዎች …ወዘተ የተሰማሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ይሁን እንጂ ክርስትናና እስልምና ከሙጡ በኋላ ቀደም ሲል ትልቅ ቦታ ይሰጣቸው የነበሩት ተሽረው ካህናትና ኡለማዎች በማኅበረሰቡ ውስጥ ከፍተኛውን ቦታ እንዲይዙ ተደርጓል፡፡ ምናልባት የአገሪቱ የቁሳዊ ሥልጣኔና ብልጽግናከአክሱም በኋላ ወደታች እየወረደ የመጣውከዚህ የዕሴት ለውጥ ጋር የተያያዘሊሆን ይችላል የሚል ግምት አለኝ፡፡
ለማጠቃለል፣የአገራችንም ሆነ የምዕራቡንዓለም የ‘ፐረኒያል’ አመለካከት ስንመለከትአንደኛ፣ሁለቱም ማለትም የኢትዮጵያው ቁዱሳን መጽሐፍትን፣ የምዕራቡ ዓለም ደግሞጥንታዊ የግሪክና የሮማውያን ድርሳናትን አይሻሩም፣ አይለወጡም፣ አይጠየቁም የሚሉ ናቸው፡፡ሁለቱም በመማር ማስተማሩሂደት ላይየአስተማሪው ድርሻ ትልቅ እንደሆነናአካላዊ ቅጣት ዋና የማስተማሪያ መሳሪያ እንደሆነም ይቀበላሉ፡፡በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፣ትምህርት ማለት መንፈሳዊና አዕምሯዊ ብቃትን ማዳበርነው፤ከሃይማኖትና ከባህል የተረከብነውን እውቀት እናጠናዋለን እንጂ ወደፊት ሌላ የዕውቀት ግኝት እናመጣለን በሚል ተስፋ ምርምር የምናካሄድበት ዘርፍ አይደለም ብለው ያምናሉ፡፡
አሁን ወዳለንበት የትምህርት ፍልስፍና በምንሄድበት ጊዜ ደግሞ፣ከ‘ኮንስታረክሽኒዝም’ና ከ‘ፕሮግረሲቪዝም’አስተሳሰቦች ጋራ የተዛመደ አመለካከት አለው ብዬ አምናለሁ፡፡ ትምህርት በይዘቱ ማኅበራዊ የኑሮ ደረጃን የሚለውጥ መሳሪያ ነው፤ማኅበረሰብን ከመለወጥ ውጪ ሌላ ፋይዳ የለውም፤በተጨማሪም የትምህርት ተቀዳሚ ትኩረት መሆን ያለበት በትምህርቱ ይዘት ላይ ሳይሆን ችግር ፈቺ ነው ወይስ አይደለም በሚለው ጥያቄ ላይ ነው፤በመሆኑም የሚመረጠው የትምህርት ዓይነት የሚወሰነው የማኅበረሰቡን ችግር ይፈታል ወይስ አይፈታም ከሚል አስተሳሰብ በመነሳት ነው፡፡ ትምህርት ተማሪውን ያማከለና የተማሪውን አጠቃላይ ፍላጎት የሚያሟላ መሆን አለበት፤ የትምህርት ሥርዓቱ በየጊዜው እንዳስፈላጊነቱ መሻሻልና መለወጥ አለበት…ወዘተ የሚሉት አመለካከቶች ከወቅቱ የአገራችን የትምህርት ፍልስፍና ጋር በእጅጉ ይዛመዳሉ፡፡ወደአገራችንሁኔታ በምንመጣበት ጊዜ፣ በማኅበረሰቡ ውስጥ ለውጥ ለማምጣት ከተፈለገ ትምህርት የልማት አጋር በመሆን መንግሥት ያቀደውን የትራንስፎርሜሽን አጀንዳ አስፈጻሚ መሆን አለበት የሚል አቋም ተይዟል፡፡
ዕንቁ፡-እስካሁን የተነጋገርንበትን ጉዳይ ማለትም ስለ ትምህርት ፍልስፍና ስለጥንታዊውና አሁን ስላለው የትምህርት ይዞታ በሚቀጥሉት ዕትሞቻችን ላይ በሰፊው እንቀጥላለን፡፡ ለአሁኑ የዛሬ ስድስት ወር ገደማ ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል ዩኒቨርሲቲ መጥተው ካነሷቸው ጉዳዮች ውስጥ ስለደሞዝ ጭማሪ የተናገሩት አስካሁን ድረስ በማነጋገር ላይ ያለ ጉዳይ ስለሆነየእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?የሚለውን ይግለጹልን፡፡
ዶ/ርዳኛቸው፡-ዩኒቨርሲቲ ከሕዝብም ሆነ ከፖለቲካ አመራሩ ክፍል የሚመጣ ሃሳብ የሚፈትሽበት፤ለማኅበረሰቡም ሆነለአስተዳደርክፍሉገንቢ አስተያየቶችንና አመለካከቶችን የሚቀርቡበት ተቋም ነው፡፡ ሆኖም ግን በአሁኑ ጊዜ በተገላቢጦሹሃሳብና ምክር ይፈልቅበታል በሚባለው ተቋም ሹመኞች በተለያየ ምክንያት እየመጡ አስተማሪዎችን እየሰበሰቡ የሃሳብና የምክር አቅራቢነትሚናመጫወታቸው በጣም ያስገርማል፡፡በተለያየ ጊዜየዩኒቨርሲቲውን መምህራን እየሰበሰቡ ከኃይማኖት እስከልማት፣ከዕድገት እስከ የውጪ ጉዳይ ፖሊሲ …ወዘተ“አሰልጣኞች” ተመድበው “ሥልጠና” ሲሰጡቆይተዋል፡፡ ይህን ጉዳይ ይበልጥ ለማብራራት በቅርቡ አቶ ብርሃኑ አስረስ ከጻፉት መጽሐፍ መጥቀስ ተገቢ ይሆናል፡፡ከታህሳሱ ግርግር በኋላጀኔራል መንግሥቱ ነዋይተይዘው ፍርድቤት በቀረበቡበት ወቅት የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሲጠየቁ “የተናቀ መንደር ‘በምንትስ’ ይወረራል”ብለው የተረቱት ተረት ሁኔታውን በሚገባ የሚገልጸው ይመስለኛል፡፡የዩኒቨርሲቲው ምሁራን ሠልጣኝ የመንግሥት ሹመኞች አሰልጣኝ የሆኑበት ግቢ ሆኗል፡፡
ዶ/ር ደብረጽዮን የደሞዝ አንሶናል ጥያቄውንሲመልሱ ‹‹እናንተ እውቀትና ክህሎት ያላችሁ በመሆናችሁ ከዩኒቨርሲቲው ውጪ ተንቀሳቅሳችሁ ተጨማሪ ገቢ ማግኘት ትላላችሁ››ብለው ነበር፡፡ መምህራንን ከተመደቡበት የማስተማር ውጪ ሌላ ተፎካካሪ ሥራ “ሥሩ”ብለውመምከራቸውና በመማር ማስተማርሂደቱ ላይ ጫና እንደሚፈጥር አለመገንዘባቸው አስገሞኛል፡፡መቼም ይኼ “ምክር” ለአብዛኞቹ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አስተማሪዎች አዲስ ነገር ሆኖ እንደማይገኝ ጥርጥርየለኝም፡፡ እኔ እስከምረዳው ድረስ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራንን “ከማስተማር ውጪ በኮንሰልታንሲም ሆነ በልዩ ልዩ መንገድ ገንዘብ ይገኛል” ብሎ መንገር ለነብር “ሚዳቋ ወይምጥንቸል ትበላላች” ብሎ እንደመምከር ይሆናል፡፡
ደሞዝን በሚመለከት ከመምህራኑ ይበልጥ በጣም እየተጎዱ ያሉት የጥበቃ፣ የጽዳት፣ የካፍቴሪያና የአትክልተኛነት ሥራዎችን የሚሰሩት ሠራተኞች ናቸው፡፡እነኚህ ሠራተኞች የሚሰሩት ሥራ ከፍተኛ ጉልበት የሚጠይቅ ሆነ ሳለ የሚከፈላቸው ደሞዝ ግን እጅግ በጣም አነስተኛ ነው፡፡ ይበልጥ የሚገርመው ደግሞ ሰባት እና ስምንትዓመታት ያህል ያገለገሉ ሠራተኞች ደሞዝ ይጨመርልናል ብለው ሲጠብቁ “ቋሚ አድርገናችኋል” በሚል ፈሊጥ የደሞዝ ቅነሳ ተደርጎባቸዋል፡፡ይኼ በእጅጉ የሚያሳዝንና ፍትሃዊነት የጎደለው እርምጃ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡በበኩሌ ዩኒቨርሲቲው አንጋፋና ትልቅ ተቋም እንደመሆኑ መጠንስሙንና ክብሩን በጠበቀ መልኩ ለእነኝህ ሰዎች ደህንነት አስቦ የደሞዝ ማስተካከያ ማድረግ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ወደጽዳት ሠራተኞች በምንሄድበት ጊዜ ደግሞ ያለው ችግር ተገቢ ደሞዝ ያለማግኘት ብቻ ሳይሆን ከጤንነትምጋር የተያያዘ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በቅርቡ ሰፋ ያለ ጽሁፍ ስለማቀርብ ለጊዜው በዚሁ ይብቃን፡፡